Tuesday, March 5, 2013

ብሉይ ኪዳን - የትንቢት ክፍል



ባለፈው ጥናታችን በብሉይ ኪዳን የሚገኙት መጻሕፍት በሥነጽሑፋዊ ይዘታቸው ከአራት እንደሚከፈሉ በመግለጽ ሦስቱን የኦሪት፣ የታሪክ እና የመዝሙርና የቅኔ ክፍሎችን አይተናል። ለዛሬ የብሉይ ኪዳን የመጨረሻ ና ፬ኛ ክፍል የሆነውን የትንቢት ክፍል ዳሰሳ እናያለን።
ትንቢት ማለት በአጭሩ ስለመጪው ሁኔታና ዘመን አስቀድሞ መናገር ነው።  ነቢያት የእግዚአብሔርን ቃል በቀጥታ ድምጽ፣ በራእይ፣ በሕልም ወዘተ… በተለያየ መንገድ በመቀበል ለሕዝቡ ያስተላልፉ ነበር። የእግዚአብሔር ሃሳብ ቃል አቀባይ ስለሆኑም ሲናገሩ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡-.. » እያሉ በማስረገጥ ነበረ። በአዲስ ኪዳን ግን ባለቤቱ ራሱ ሰው ሆኖ በመምጣት ፊት ለፊት « እኔ እላችኋለሁ..» እያለ መናገሩን እናስታውሳለን።
በትንቢት ክፍል ውስጥ በስማቸው ራሱን የቻለ መጽሐፍ ካላቸው ነቢያት ውጭ በብሉይ ኪዳንም ሆነ በአዲስ ኪዳን ሌሎች ብዙ ነቢያት የተነሱ መሆኑ ይታወቃል፤ ለምሳሌ ከብሉይ ኪዳን እንደ ሙሴ፣ ሰሙኤል፣ ዳዊት፣ ኤልያስ፣… ከአዲስ ኪዳን እንደ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ወንጌላዊው ዮሐንስ (በዮሐንስ ራእይ) እነዚህ ሁሉ ትንቢቶችን ተናግረዋል።
የትንቢት መጻሕፍቱ በብሉይ ኪዳን መጨረሻ በአንድ ላይ ቢቀመጡም ነቢያቱ ትንቢቶችን የተናገሩት ግን በአብዛኛው በመጽሐፈ ነገሥት ታሪክ ውስጥ ነበር። የትንቢት መጻሕፍት ይዘት በወቅቱ እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ከእስራኤላውያን ጋር ባደረገው ቃል ኪዳን (ብሉይ ኪዳን) ሁኔታ ጋር የተያያዘ ነበር። የተሰጣቸውን የቃል ኪዳን ትእዛዝ ከጠበቁ ስለሚያገኟቸው በረከቶች፣ ትእዛዛቱን እንዳይጥሱ የተለያዩ  ማስጠንቀቂያዎችና ትእዛዛቱን ከጣሱ ስለሚያገኛቸው ቅጣቶች ይናገራሉ። ከዚህ ሌላ ስላለፈው ዘመን፣ ስለመጪው ዘመን፣ ስለአዲስ ኪዳን፣ ስለ ክርስቶስ የሚናገሩት የትንቢት ክፍሎች አሉ። አብዛኛው የትንቢት ክፍል ይዘት ግን ከወቅቱ የእስራኤላውያን ሁኔታ ጋር የተያያዘ እና በአሁኑ ሰዓትም ፍጻሜን  ያገኘ ነው። የትንቢቶችን ይዘት በተናገሩባቸው ዘመናት ብንከፍላቸው እንደሚከተለው በሦስት ዘመናት ማየት ይቻላል።