Wednesday, September 26, 2012

ብርሃን ይሁን፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር የመጀመሪያው ቃል (ንግግር)
Birhan Yihun, sebket, READ IN PDF
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ ብርሃንም ሆነ። ዘፍ ፩፡፫
በመጽሐፍ ቅዱሳችን በመጀመሪያው መጽሐፍ በመጀመሪያው ምዕራፍ እግዚአብሔር በመጀመሪያ የተናገረው ቃል ብርሃን ይሁን የሚል ነው። ከዚያ በፊት ባሉት ቁጥሮች በዝምታ (በአርምሞ) ሲሠራ ቆይቷል። ሰማይ፡ ምድር፡ ጨለማ፡ መላእክት…. የተፈጠሩት በዝምታው ነው። እግዚአብሔር በዝምታውም ይሠራል። በኀልዮ ይላሉ፡፡ ሲያስብ ይፈጸማል፡ ይከናወናል። የሰው ሃሳብ ምናባዊ የሆኑ ብዙ ነገሮችን ሊያወጣ ሊያወርድ ይችላል። እግዚአብሔር ግን በሃሳቡ ብቻ ተጨባጭ ነገሮችን ያስገኛል።  ታላላቆቹና የፍጥረታት መሠረታውያን የተባሉት ፬ቱ ባሕርያት እሳት፡ ነፋስ፡ ውኃ፡መሬት የተፈጠሩት በኀልዮ፡ (በዝምታ) ነው።
እግዚአብሔር በምን ተናገረ?
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ። እግዚአብሔርም… አለ። ይህ የተናገረበት ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነው አካላዊ ቃል ወልድ በኋላም ሰው የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። እግዚአብሔር በሦስትነቱ ሥላሴ ሲባል አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው። ሥላሴ በአብ ልብነት ያስባሉ፡ በወልድ ቃልነት ይናገራሉ፡ በመንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሕያው ሆነው ይኖራሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር ዓለምን ሲፈጥር የተናገረበት ቃል ወልድ ነበረ።
በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ዮሐ ፩፡ ፩።
ያ ቃል ወልድ በሐዲስ ኪዳን ሥጋን ለብሶ ሰው የሆነው፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው፡ ዓለምን ሁሉ ያዳነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።  ….. ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ዮሐ ፩፡ ፲፬።

ዛሬ እግዚአብሔር በምን ይናገራል?  
- በብሉይ ኪዳን በዝምታ፡ በሕልም፡ በራእይ፡ በነቢያት፡…. በወልድ ቃልነት ይናገር ነበር።
ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ዕብ ፩፡፩
-በሐዲስ ኪዳን የሚያናግርበት መንገድ አንድ ብቻ ነው።
ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን።  ዕብ ፩፡፪
እንግዲህ እግዚአብሔር ዛሬ እኛን የሚያናግረን በዚያው ቃል - በወልድ - በኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህንም የምናውቀው በተጻፈው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ እና በመምህራን አማካይነት ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር የሚያናግረንን ለማወቅ፡ ብሎም ለመታዘዝ ቃሉን - ይሄውም ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን እና መጽሐፍ ቅዱስን - ማወቅ አለብን ማለት ነው። ይህ ቃሉ ዓለምን የፈጠረ - ፈጣሪ፡ ዓለምንም ያዳነ - አዳኝ ዛሬም የእኛን ሐይወት ያዳነ- የሚሠራ አካላዊ ቃል ነው። እግዚአብሔር ሲያናግረን ልናዳምጥና ልንጠቀምበት ይገባል።

Monday, September 17, 2012

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካዊ ዳሰሳ - አዲስ ኪዳን


ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችን አጠቃላይ ግንዛቤ ይረዳን ዘንድ በሁለቱ ኪዳናት ያሉትን ታሪኮች ጠቅለል አድርገን ለማየት የብሉይ ኪዳንን ታሪካዊ ፍሰት ባለፈው ትምህርታችን ማየታችን ይታወሳል። ለዛሬ የአዲስ ኪዳንን አጠቃላይ ይዘት እንዲሁ እንመለከታለን።
አዲስ ኪዳንን አዲስ ያሰኘው ብሉይ ኪዳን ያለፈ፣ ያረጀ ወይም የቆየ ስለሆነ ነው። ብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ጋር የገባው ቃል ኪዳን ሲሆን በእነርሱ አለመታዘዝ ምክንያት ኪዳኑ ሊጸኛ አልቻለም።
«ፊተኛው ኪዳን ነቀፋ ባይኖረው፥ ለሁለተኛው ስፍራ ባልተፈለገም ነበር።…. አዲስ በማለቱ ፊተኛውን አስረጅቶአል፤ »  ዕብ ፯፣ ፯ና ፲፫።
እስራኤላውያን እንታዘዛለን ብለው ቃል የገቡበትን ሕግ ሊያከብሩ ባለመቻላቸውና ሕጉን በመጣሳቸው እግዚአብሔር በዚያው በብሉይ ኪዳን ዘመን ሌላ አዲስ ኪዳን እንደሚመሠርት መናገሩን ካሁን ቀደም ጠቅሰን መማማራችን ይታወሳል። ዘጸ ፳፬፣፯።
« እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር፦ ኤር ፴፩ ፣ ፴፩ - ፴፬
አዲስ ኪዳን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን መላውን ዓለም /የሰው ዘር የሚመለከት እግዚአብሔር በልጁ ሞት ለሰው ያደረገው የቸርነቱን ሥራ የሚያሳይ ኪዳን ነው።
እንዲሁም ከእራት በኋላ ጽዋውን አንሥቶ እንዲህ አለ፦ ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው። ሉቃ ፳፪፣፳።
ካሁን ቀደም እንዳየነው ብሉይ ኪዳን ስለአንድ ሕዝብ - ስለ እስራኤላውያን ይናገራል፤ አዲስ ኪዳን ግን ስለ አንድ ሰው - ስለኢየሱስ ክርስቶስ ይናገራል። ስለዚህ መላው አዲስ ኪዳን ከክርስቶስ ምጽአት እስከ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት ይናገራል ማለት ነው። አዲስ ኪዳን በሥነ ጽሑፋዊና ትምህርታዊ ይዘቱ ወንጌል፣ ታሪክ፣ መልእክትና ትንቢት ተብሎ ከአራት ይከፈላል።
ወንጌል ማለት የምሥራች ቃል ነው። ይህም ወንጌል ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

«ይህም ወንጌል በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ በኃይል የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስለ ተገለጠ ስለ ልጁ ነው፤ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።» ሮሜ ፩፣፫-፬።

Friday, September 7, 2012

በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ


ይህን ቃል የምናገኘው በመዝሙረ ዳዊት መዝ ፷፭፣ ቁጥር ፲፩ ላይ ነው።  «በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።» በግዕዙ «ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ - የምሕረትህን ዓመት አክሊል ትባርካለህ» ይላል።
በቸርነትህ፡- እግዚአብሔር የዓለማት እና የዘመናት ፈጣሪ፡ ብቻ ሳይሆን አስተዳዳሪም ነው። ዓለማት የተፈጠሩት፣ ዘመናት የሚቆጠሩት በቸርነቱ ነው። ማንም ሰው በዚህ ሃገር፣ በዚህ ዘመን ልፈጠር ብሎ ሃሳብ አላቀረበም። የሕልውናችን ምንጩ ቸርነቱ ነው። የተፈጥሮ ዑደት፣ የዘመናት መፈራረቅ፡ የዕፅዋት ዕድገት፣ የእንስሳት ሕይወት… ሁሉ የቸርነቱ ውጤት ነው። አንድ መምህር «ክረምቱ የሚገባው በባለሥልጣኖች ፊርማ ቢሆን ኖሮ ዝናብ ሳይጥል ኅዳር ታኅሳስ ይሆን ነበር።» ብሏል፤ እግዚአብሔር ከመላው ፍጥረት እና ከሕይወት ጋር የተያያዙትን ነገሮች በራሱ ብቻ ቁጥጥር ሥር አድርጓቸዋል። ፀሐይ የምትወጣው፣ ክረምት የሚገባው፣ እህሉ የሚበቅለው…. በቸርነቱ ነው። እኛ ክፉ ብንሆንም፣ በኃጢአት ብንጸናም፡ የእርሱ ቸርነት አልተቋረጠችም። የእግዚአብሔርን መጋቢነት ከኛ ደግነት/ክፋት ጋር የሚያገናኘው ነገር ስለሌለ እርሱ ሁልጊዜም ፍጥረቱን መመገቡን አያቋርጥም። እግዚአብሔር ሰውን ፈጥሮ ሰውም እየበዛ ሲሄድ በዚያው ልክ ክፋቱ በመብዛቱ በኖኅ ዘመን አንድ ጊዜ ምድርን ካጠበ በኋላ የተናገረው ቃል እንዲህ ይላል፡-
«በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፥ ብርድና ሙቀት፥ በጋና ክረምት፥ ቀንና ሌሊት አያቋርጡም።» ዘፍ ፰፣፳፪።
የሰው ልጅ ክፋት ቢበዛም ቸርነቱ እንዳልተቋረጠች ያሳያል፤ አሁንም እንደዚያው ነው። እርሱ እግዚአብሔር አይለወጥምና። ዛሬም ቸርነቱ ስላልተቋረጠ ሕልውናውን ለካዱት እንኳ ሳይቀር ፀሐይን ያወጣል፣ ዝናብን ያዘንባል።
«…እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና።» ማቴ ፭፣፵፭።
የቸርነቱን ነገሮች ዘርዝረን አንጨርሰውም።