Thursday, August 30, 2012

መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢትና የዓለም ፍጻሜ-ክፍል ፪


ባለፈው ክፍል የዓለምን ፍጻሜ አመላካች የሆኑ ከአሁን ቀደም እኔ ክርስቶስ ነኝ ብለው የተነሱ ሃሰተኞችን እንዲሁም በየቦታው እስከዛሬ የተካሄዱ ጦርነቶችን መረጃዎች ማየታችን ይታወሳል። ዛሬም ይህንኑ መረጃ ከመጽሐፍ ቅዱስ ምን ያህል እየተፈጸመ እንደሆነ እናያለን።
ማቴ ፳፬፣፯… ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤
ራብም፡
ከየትኛውም ዘመን ይልቅ በያዝነው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች በተለይ በታዳጊ ሃገሮች የሚገኙ ወገኖች በከፍተኛ ደረጃ በረሃብ እየተጠቁ መሆኑ ከማንም የተሰወረ አይደለም። የዓለማችን የሃብት ክፍፍል እና የሕዝቦች ስብጥር ሲነጻጸር ምን ያህል ፍትሐዊ እንዳልሆንን ያሳያል። መረጃዎች እንደሚያሳዩት 80%  የሚሆነው የምድራችን ሃብት 20% በሆነው የዓለም ሕዝብ እጅ ይገኛል። የሚከተሉት እውነታዎች የዓለም የምግብ ፕሮግራም /World Food Program/  በተለያዩ ጊዜያት ካወጣቸው መረጃዎች የተወሰዱ ናቸው።
-      እ.ኤ.አ በ2009 ዓ/ም ከአንድ ቢሊየን በላይ የሚሆን ሕዝብ በቂ ምግብ ማግኘት አልቻለም። ይህም ማለት የአሜሪካ፡ የአውሮፓ እና የካናዳ ሕዝብ ቢደመር እንኳ ይህን ያህል አይሆንም። በወቅቱ ከዓለማችን ከ6 ሰው አንዱ ለረሃብ የተጋለጠ ነበር ማለት ነው፡፡ ከእነዚህም 90 በመቶ በላይ የሚገኘው በታዳጊ ሃገራት ውስጥ ነው።
-      ከምግብ እጥረት ጋር በተያያዘ ምክንያት በየቀኑ 25 ሺ ሕጻናት እና ወጣቶች ለህልፈት ይዳረጋሉ።
-      ከግማሽ በላይ የሚሆነው የዓለም ሕዝብ የሚኖርባቸው እስያ እና የፓሲፊክ አካባቢዎች በዓለም ከሚገኙት በረሃብ ከተጠቁት 2/3 ኛው ይገኝባቸዋል።
-      በአሁኑ ሰዓት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት /malnutrition/ ከኤች አይ ቪ/ኤድስ፡ ከቲቢ እና ከወባ ከሶስቱም ድምር በላይ ሕጻናትን እየቀጠፈ ያለ የዓለማችን ችግር ነው። ከአራት ሕጻናት አንዱ የተመጣጠነ ምግብ አያገኝም። በታዳጊ ሃገራት ከ10 ሚሊየን በላይ ለሚሆነው የሕጻናት ሞት 60 በመቶ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ከ9 ሚሊየን በላይ ለሆነው ከአምስት ዓመት በታች ባሉ ሕጻናት ለደረሰው የሞት አደጋ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ይህ ማለት በየ6 ሴኮንድ አንድ ሕጻን ይሞታል ማለት ነው።
-      ከዓለማችን ሕዝብ ከ7 ሰው አንዱ ራቱን ሳይበላ ይተኛል።…….

Sunday, August 26, 2012

የጥያቄ፩- መልስ


 1.  እግዚአብሔር  አዳምን  ከመፍጠሩ  በፊት  አዳም  እንደሚሳሳት ያውቃል/አያውቅም?  እንደሚሳሳት  ካወቀ ለምን  ፈጠረው?  
  ወደጥያቄው መልስ ከመግባታችን በፊት ስለእግዚአብሔር ና ስለ ሰው ባሕርያት በጥቂቱ ማወቅ  ያለብን ጉዳይ አለ። እግዚአብሔር የማይመረመር፡ ልዑልና ኃያል አምላክ ስለሆነ ስለራሱ የገለጠልንን ያህል ብቻ እናውቃለን እንጂ ሙሉ በሙሉ ልንደርስበት አንችልም። የሰው ልጅ በሁለንተናው ውሱን ነው። ዓይናችን የሚያይበት፡ ጆሮአችን የሚያደምጥበት፡ እጃችን የሚዘረጋበት…. ሁለንተናችን ገደብ አለው።   ስለፈጣሪ ማወቅ አይደለም ስለፍጥረታት እንኳን ገና ያልደረስንባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ስለሆነም በአስተሳሰባችን ተነስተን የእግዚአብሔርን ሃሳብና አሠራር እንዲህ ቢሆን እንዲህ ይሆናል ብለን የራሳችን ግምት ልንወስድ አንችልም። ከውስንነታችን የተነሳ።

Friday, August 17, 2012

ጥያቄ-፩


    /ሜ የቀበ/
ይህ ክፍል መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆኑ ጥያቄዎችን የምንወያይበት ነው። 
    
      ፩. እግዚአብሔር  አዳምን  ከመፍጠሩ  በፊት  አዳም  እንደሚሳሳት ያውቃል/  አያውቅም? እንደሚሳሳት  ካወቀ ለምን  ፈጠረው?  
    
     ለዚህ ጥያቄ ተሳታፊዎች ከዚህ ጽሑፍ ሥር comments የሚለውን በመጫን post comment በሚለው  መላክ ትችላላችሁ። 

Thursday, August 9, 2012

ሚዛናዊነት

Mizanawinet, sebket, READ IN PDF


የሕይወታችን መመሪያ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን ስናጠና ከምንረዳቸው ታላላቅ ቁምነገሮች አንዱ ሚዛናዊነት ነው።በውስጡ ታሪካቸው ስለሰፈረላቸው ሰዎች መልካም ተግባር ሲነግረን ደካማ የሕይወት ክፍላቸውንም ያስነብበናል።
ለምሳሌ፡-
o   የአብርሃም የእምነት አባትነትና  ------በእግዚአብሔር ፊት የነበረበትን መንፈሳዊ ድክመት
o   የዳዊትን እንደልቤነትና ----- የዝሙት ውድቀት
o   የሙሴን ጠንካራ መሪነትና---- የእምነቱን መዛል  እናነባለን።
ከውድቀታቸው እንድንማር ብርታታቸውን አርአያ እንድናደርግ መንፈስ ቅዱስ ይህን አድርጓል።
በእኛ ዘንድ ግን እንዲህ አይደለም። ብናወራና ቢወራልን የምንወደው የበረታንበትን ነገር ብቻ ነው። ለዚህም ይመስላል ቆመው አይደለም ሞተው እንኳ ስለድክመታቸው እንዲወራ በማይፈልጉ ሰዎች ምክንያት በየቀብር ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የሚነበበው የሕይወት ታሪክ የጥቂት እውነትና የብዙ ውሸት ድምር ውጤት የሚሆነው።

ክርስቲያን ግን የእውነትና የማመዛዘንን በረከት የተረዳ ነው።
በአዲስ ኪዳንም ከኃጢአት በቀር በክርስቶስ ሕይወት የምንመለከተው ይህንኑ ነው።
o   የብዙዎችን የልብ ስብራት ከአፉ በሚወጣው የሕይወት ቃል ጠግኗል።  ----- ባልተቀበሉትና ባላወቁት አፍም ተሰድቧል።
o   በምራቁ  አፈር ለውሶ በደረቅ ግንባር ላይ ዓይን ፈጥሯል። ----- ርኅራሄ በሚነበብበት ፊቱ ላይም ምራቅ ተተፍቶበታል።
o   ጎባጣ አቅንቷል። ----- ጀርባው እስኪላጥ ተገርፎአል
o   የሞቱትን ከመግነዝ ፈትቶ ከመቃብር አስነስቷል። ------ በአደባባይ ተሰቅሎ ስለሁላችንም ሞቷል።
ይህም (ሚዛናዊነት) በቃሉ ውስጥ ያለማዳለል ሰፍሮልናል።
   ብዙ ሕመምን ያስከተሉ ነገሮች ያላቸው መልካም ጎን ቢታወቅ ኖሮ ሀሴትን ይፈጥሩ ነበር። ሁሉም ነገር መልካምና መጥፎ ጎን ሲኖረው ቁም ነገሩ ያለው ግን ነገሮችን በመልካም ጎናቸው መጠቀሙ ላይ ነው። የአንድ ነገር ገጽታ እንደ ተመለከትንበት አቅጣጫ ይወሰናል። ስለዚህ ነገሮችን በሚዛናዊነት እንመልከታቸው።
                               « በሚጠሉኝ መሀል የሚወደኝን አገኘሁት» ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ- ገጽ
                                                                                           በዲ/ ኢዮብ ይመር
የአንድን ነገር ሙሉ ገጽታ የምናገኘው ከሁሉም አቅጣጫ (በሚዛናዊነት) ስንመለከተው ነው።
በሥነ-ሕንጻ ትምህርት አራት መሠረታዊ እይታዎች አሉ፡ - የፊትለፊት፡ የጎን፡ የላይና የውስጥ (Front, side, top and section views) ስለዚያ ሕንጻ የተሟላ ስእል (ምስል) ለማግኘት እነዚህን አራቱንም አቅጣጫዎች  በሙሉ ማየትና መረዳት ያስፈልጋል።
ተፈጥሮአችን ራሱ ሚዛናዊ እንድንሆን ያስተምረናል። ሁላችንም በተቃራኒ  አቅጣጫ የተቀመጡ ሁለት ጆሮዎች አሉን። አእምሮአችን (ሕሊና) እና አንደበታችን (አፍ) ግን አንድ ነው። ስለአንድ ጉዳይ ተቃራኒ የሆኑ ብዙ ነገሮችን ልንሰማ እንችላለን።
 ስለአንድ ነገር በአንደበታችን ከመናገራችን በፊት ነገሮችን በማስተዋል አመዛዝነን ከግራ ከቀኝ መርምረን ቢሆን አድማጭን ከሚያቆስል ንግግር እንጠበቃለን፡ ራሳችንንም ከፍርድ እንጠብቃለን።
በስፍራም፡ በአቅጣጫም  የማይወሰነው እግዚአብሔር  ከላይ ሆኖ ሁሉን ፍጹም በሆነ ሚዛናዊነት ይመለከታል። እኛ በየተመለከትንበት አቅጣጫ ፍርድን ብናዛባ፡ ሁሉም በእርሱ ፊት ግልጽ ነውና በፍትሐዊነቱ ፍርድን ያደላድላል።
ስለዚህ በምንሰማቸው ብዙ ነገሮች ሚዛናዊነት ይኑረን።  ሳናመዛዝን ለመናገርም አንቸኩል። ሁላችንም ሁሉም በእግዚአብሔር ፊት በግልጽ የሚታይ ነውና።
« እግዚአብሔር በሰማይ አንተም በምድር ነህና በአፍህ አትፍጠን። በእግዚአብሔርም ፊት ቃልን ይናገር ዘንድ ልብህ አይቸኩል፡ ስለዚህም ቃልህ ጥቂት ትሁን።» ምሳ ፭፡፪።