Friday, November 15, 2013

አዲስ ኪዳን - የትንቢት ክፍል (የዮሐንስ ራእይ)

በአዲስ ኪዳን ዳሰሳ ባለፈው በ፫ኛው ጥናታችን የመልእክት ክፍል የሚለውን የቅዱስ ጳውሎስንና ቀጣዮቹን መልእክታት ዳሰሳ አይተናል። ዛሬ በአዲስ ኪዳን የመጨረሻ የሆነውን የትንቢት ክፍል ይሄውም የዮሐንስ ራእይን ጠቅለል አድርገን እንመለከታለን። የዮሐንስ ራእይ የመጽሐፍ ቅዱስ የመጨረሻው ክፍል ሲሆን በአዲስ ኪዳን መጀመሪያ ክርስትና በሐዋርያት በኩል ወደ ዓለም ከተስፋፋ በኋላና የተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት (የክርስቲያኖች ኅብረት) ከተመሠረቱ በኋላ እነርሱን ለማበረታታት፣ በተለያየ ምክንያት ከክርስትና ወደ ኋላ ያሉትንም ለመገሰጽ፣ በዓለም ላይ በክርስቲያኖች የሚደርሰው መከራና ፈተና ፍጻሜ እንደሚኖረው ዲያብሎስም ለመጨረሻ ጊዜ ድል እንደሚደረግ የመሳሰሉ ሃሳቦችን ይዟአል።
መጽሐፉ የዮሐንስ ራእይ ቢባልም ራእዩ ከመጽሐፉ መጀመሪያ እንደምንረዳው እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የገለጠለት ሆኖ በመልአክ በኩል ለዮሐንስ ልኮለት የጻፈው ነው።   
« ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥» ራእ ፩፣፩
መጽሐፉ የአዲስ ኪዳን ትንቢት እንደመሆኑ መጠን ከብሉይ ኪዳን እንደ ሕዝቅኤልና ዳንኤል ካሉ አንዳንድ የትንበት መጽሐፍ ጋር ያሉ ጉዳዮችን እያነሳ ይናገራል። በወቅቱ በሐዋርያት እና በተከታዮቻቸው ትምህርት ለተመሠረቱ የተለያዩ የክርስቲያኖች ኅብረት በተለይም በእስያ ለሚገኙ ፯ አብያተ ክርስቲያናት ማጽናኛ እና ተግሣጽ ሆኖ ሲጻፍ እንደ አጠቃላይ በመጨረሻው ዘመን ለሚገኙ ክርስቲያኖችም ተስፋና ማጽናኛ ምክሮችን ይዟል። አቀራረቡ ከሌሎች በተለየ በስእላዊ መግለጫዎች የተሞላ ድራማ መሰል ሥነ-ጽሑፍ ነው። ስለመጨረሻው ዘመን ብዙ ትንቢቶችን እንደያዘ እና ረቂቅ ምሥጢራዊ የአጻጻፍ ስልት እንዳለው ብዙ መምህራን ያስረዳሉ። በዚህም ምክንያት በመጽሐፉ አተረጓጎም ላይ ብዙ የተለያዩ ሃሳቦች ይቀርባሉ።
ዮሐንስ ቀደም ሲል በወንጌሉ ኢየሱስ ክርስቶስን «የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ» ብሎ ካስተዋወቀ በኋላ አሁን ደግሞ በራእዩ የታረደው በግ ይለዋል። (ዮሐ ፩፣፳፱ ፡ ራእ ፭፣፲፪)። ሞትን ድል አድርጎ ከተነሳ በኋላም ድል የነሳው የዳዊት ስር የይሁዳ አንበሳ ተብሏል። ለዓለም ሁሉ ኃጢአት ቤዛ ሆኖ በመስቀል ላይ የዋለው ስለ ሁላችን የሞተው የታረደው በግ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ በትንቢተ ኢሳይያስ በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ የተባለለት በዚህ መጽሐፍ የድል አድራጊነቱን ውጤት የበጉ ደም፣ የበጉ የሕይወት መጽሐፍ፣የበጉ ሠርግ፣ የበጉ ሙሽራ፣ የበጉ ዙፋን ወዘተ… በማለት በተለያየ መልክ ይገልጻል።

Saturday, November 9, 2013

አዲስ ኪዳን - የመልእክት ክፍል

ባለፈው ጥናታችን በአዲስ ኪዳን የታሪክ ክፍል የተባለውን የሐዋርያት ሥራን አጠቃላይ ዳሰሳ አይተናል። ዛሬ በመቀጠል የአዲስ ኪዳን ፫ኛ ክፍል የሆነውን የመልእክታት አጠቃላይ ዳሰሳ እናያለን። የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት የተቀመጡት በታሪካዊ ፍሰታቸው ቅደም ተከተል እንደመሆኑ መጠን በቅድሚያ በወንጌል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ከልደት እስከ ሞትና ትንሣኤ የፈጸመውን የቤዛነት ሥራ፡ በመቀጠል ተከታዮቹ የነበሩት ሐዋርያት ይህን ወንጌል ወደ ዓለም ለማዳረስ ቤተ ክርስቲያንን በመመሥረት የፈጸሙት ሥራ በተለይ የጴጥሮስና የጳውሎስ ተልዕኮና ስብከቶች በሐዋርያት ሥራ ተዘግቧል። በማስከተል እነዚሁ ሐዋርያት የመሰረቷቸውን አብያተ ክርስቲያናት /የክርስቲያኖች ኅብረት/ ለማጠናከር በሩቅ ሆነው ደብዳቤ /መልእክት/ በመጻፍ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ያሳድጓቸው ነበር።
የመልእክት ክፍል ልዩ መልእክታትና አጠቃላይ መልእክታት ተብለው በሁለት ሊከፈሉ ይችላል።  ልዩ መልእክታት የሚባሉት ሰፊውን ክፍል የሚይዙት የጳውሎስ መልእክታት ሲሆኑ ከሮሜ እስከ ዕብራውያን ያሉት ፲፬ መልእክታት ናቸው፤ ልዩ ያሰኛቸውም በወቅቱ ለታወቁ አብያተ ክርስቲያናት (ኅብረቶች) እና ግለሰቦች በተወሰኑ ርዕሰ ጉዳዮች ስለጻፈላቸው ነው። /የዕብራውያን መልእክት የጳውሎስ ይሁን አይሁን በመጽሐፍ ቅዱስ መምህራን አከራካሪ ጉዳይ ነው። አጻጻፉ ከሌሎች መልእክታት ይለያል።/ አጠቃላይ መልእክታት የሚባሉት ጌታ በተለያዩ ጉዳዮች ከሌሎች ለይቶ ሲያቀርባቸው የነበሩት የ፫ቱ የጴጥሮስ፣ የዮሐንስ፣ የያዕቆብ እና የይሁዳ በጠቅላላ ፮ መልእክታት ሲሆኑ እነዚህ መልእክታት ጠቅለል ያለ ጉዳይ የያዙ እና በወቅቱ ለሁሉም አማኞች የተጻፉ ነበሩ። ይሁንና ሁሉም መልእከታት ዛሬ እግዚአብሔር ለኛ የሚያስተላልፋቸውን ጉዳዮች የያዙ መሆናቸውን ወደፊት በጥናታችን በየተራና በሰፊው  የምናየው ይሆናል።

Wednesday, October 16, 2013

አዲስ ኪዳን - የታሪክ ክፍል (የሐዋርያት ሥራ)

ባለፈው ክፍል በጀመርነው የአዲስ ኪዳን ዳሰሳ የወንጌል ክፍልን ማየታችን ይታወሳል። በዚህም ወንጌል ማለት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ ሕይወት ከልደት እስከ ሞትና ትንሣኤ በአራቱ ወንጌላውያን የተዘገበው የመጽሐፍ ቅዱስ የምሥራች ቃል መሆኑን ተመልከተናል። በመቀጠል ይህ ወንጌል በሐዋርያት በኩል እንዴት ወደ ዓለም መሰራጨት እንደጀመረ በአዲስ ኪዳን የታሪክ ክፍል በሚባለው በሐዋርያት ሥራ ተዘግቦ የምናገኘው ሲሆን ለዛሬ ይህን እናያለን።
የሐዋርያት ሥራ ስሙ እንደሚነግረን ሐዋርያት የሠሩት ወንጌል የማስፋፋት ሥራ ነው። ሐዋርያት በአንድነት መንፈስ ለአንድ የተቀደሰ ዓላማ በጽናት እንደሠሩ እናያለን። ይህ ኅብረታቸው ቤተ ክርስቲያን ይባላል። የቤተክርስቲያን ቀዳሚ ትርጉም የክርስቲያኖች ኅብረት /አንድነት/ ነው። መጽሐፉ በሐዋርያት የተመሠረተችው የመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን (ኅብረት) የነበራትን የአገልግሎት ትጋት ያሳየናል። የወንጌል ስብከትና መስፋፋት፣ ጸሎት፣ የጋራ የፍቅር ማዕድ (አጋፔ)፣ ሃብትና ንብረታቸውን በጋራ መጠቀም፣ የተቸገሩትን መርዳት፣ ድውያንን መፈወስ፣ የሥራ ክፍፍል /አስተዳደራዊ መዋቅር፣ በመሳሰሉት መንፈሳዊ አገልግሎቶች  እናያለን።
ከዚህም ጋር ከነበራቸው ጠንካራ አገልገሎት ጎን ለጎን ይደርስባቸው የነበሩ ፈተናዎች ነበሩ። ከአይሁድ የሚደርስባቸው ስደት፣ እንደ ሐናንያና ሰጲራ ካሉ ራስ ወዳዶች የሚመጣው ስስት፣ ከአይሁድ ጋር ስለነበራቸው የእምነት ግጭት፣ በውስጥ አስተዳደራዊና ቀኖናዊ ልዩነቶች ወዘተ የመሳሰሉ… ተግዳሮቶችን እንዳስተናገዱ ይታያል። ሐዋርያቱ ከፍተኛ የሆነ የወንጌል አገልግሎት ሥራ የሠሩት በከፍተኛ ተግዳሮት ውስጥ እያለፉ ስለነበር ምንጊዜም ዛሬም ከተሳካ አገልግሎት ጋር የከረረ ተቃውሞ የማይቀር መሆኑን እንገነዘባለን።

Sunday, May 5, 2013

አዲስ ኪዳን - የወንጌል ክፍል



ከአሁን ቀደም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችን የብሉይ ኪዳንን ዳሰሳ በየክፍሎቹ ማለትም በኦሪት፣በታሪክ፣ በቅኔና መዝሙራት እንዲሁም በትንቢት ክፍል ይዘታቸውን በአጭር በአጭሩ ማየታችን ይታወሳል። አሁን ደግሞ በአዲስ ኪዳን ያሉትን ክፍሎች ማለትም የወንጌል፣ የታሪክ፣ የመልእክትና የትንቢት ክፍሎችን እንዲሁ በየተራ እንዳስሳለን። ለዛሬ የወንጌል ክፍልን እናያለን።
የወንጌል ክፍል የሚባሉት አራቱ ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስና ዮሐንስ እንደሆኑ ይታወቃል። ወንጌል ማለት ምን ማለት ነው? ስንል ወንጌል ማለት የምሥራች ማለት ነው። በኃጢአት ለተያዘው የሰው ዘር መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ መወለዱን…መሞቱን እና መነሳቱን የሚገልጽ የደስታ ቃል ማለት ነው። ከአንድ ወንድሜ እንደተማርኩት ወንጌል ማለት የምስራች መሆኑን ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚተረጉምልን እነዚህን ሁለት ጥቅሶች ማየት እንችላለን።
አስቀድሞ በነቢዩ በኢሳይያስ ስለ ክርስቶስ የተነገረው እንዲህ ይላል።
የጌታ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር ቀብቶኛልና ልባቸው የተሰበረውን እጠግን ዘንድ፥ ለተማረኩትም ነጻነትን ለታሰሩትም መፈታትን እናገር ዘንድ ልኮኛል። የተወደደችውን የእግዚአብሔርን ዓመት አምላካችንም የሚበቀልበትን ቀን እናገር ዘንድ፥ የሚያለቅሱትንም ሁሉ አጽናና ዘንድ» ኢሳ ፷፩፣፩-፪
ይህንኑ ክፍል ሉቃስ በወንጌል ሲጠቅሰው እንዲህ ይላል።
« የነቢዩንም የኢሳይያስን መጽሐፍ ሰጡት፥ መጽሐፉንም በተረተረ ጊዜ። የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩትም መፈታትን ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፥ የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል ተብሎ የተጻፈበትን ስፍራ አገኘ።»  ሉቃ ፬፣ ፲፯-፲፱።
ነቢዩ ኢሳይያስ የምስራች ያለውን ወንጌላዊው ሉቃስ ወንጌል ብሎ ይተረጉመዋል። ስለዚህ ወንጌል ማለት የምሥራች ማለት ነው። ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ያለው የምሥራች ወንጌል ነው። እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ወንጌል ማለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ያብራራል።

Tuesday, March 5, 2013

ብሉይ ኪዳን - የትንቢት ክፍል



ባለፈው ጥናታችን በብሉይ ኪዳን የሚገኙት መጻሕፍት በሥነጽሑፋዊ ይዘታቸው ከአራት እንደሚከፈሉ በመግለጽ ሦስቱን የኦሪት፣ የታሪክ እና የመዝሙርና የቅኔ ክፍሎችን አይተናል። ለዛሬ የብሉይ ኪዳን የመጨረሻ ና ፬ኛ ክፍል የሆነውን የትንቢት ክፍል ዳሰሳ እናያለን።
ትንቢት ማለት በአጭሩ ስለመጪው ሁኔታና ዘመን አስቀድሞ መናገር ነው።  ነቢያት የእግዚአብሔርን ቃል በቀጥታ ድምጽ፣ በራእይ፣ በሕልም ወዘተ… በተለያየ መንገድ በመቀበል ለሕዝቡ ያስተላልፉ ነበር። የእግዚአብሔር ሃሳብ ቃል አቀባይ ስለሆኑም ሲናገሩ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡-.. » እያሉ በማስረገጥ ነበረ። በአዲስ ኪዳን ግን ባለቤቱ ራሱ ሰው ሆኖ በመምጣት ፊት ለፊት « እኔ እላችኋለሁ..» እያለ መናገሩን እናስታውሳለን።
በትንቢት ክፍል ውስጥ በስማቸው ራሱን የቻለ መጽሐፍ ካላቸው ነቢያት ውጭ በብሉይ ኪዳንም ሆነ በአዲስ ኪዳን ሌሎች ብዙ ነቢያት የተነሱ መሆኑ ይታወቃል፤ ለምሳሌ ከብሉይ ኪዳን እንደ ሙሴ፣ ሰሙኤል፣ ዳዊት፣ ኤልያስ፣… ከአዲስ ኪዳን እንደ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ወንጌላዊው ዮሐንስ (በዮሐንስ ራእይ) እነዚህ ሁሉ ትንቢቶችን ተናግረዋል።
የትንቢት መጻሕፍቱ በብሉይ ኪዳን መጨረሻ በአንድ ላይ ቢቀመጡም ነቢያቱ ትንቢቶችን የተናገሩት ግን በአብዛኛው በመጽሐፈ ነገሥት ታሪክ ውስጥ ነበር። የትንቢት መጻሕፍት ይዘት በወቅቱ እግዚአብሔር በሙሴ በኩል ከእስራኤላውያን ጋር ባደረገው ቃል ኪዳን (ብሉይ ኪዳን) ሁኔታ ጋር የተያያዘ ነበር። የተሰጣቸውን የቃል ኪዳን ትእዛዝ ከጠበቁ ስለሚያገኟቸው በረከቶች፣ ትእዛዛቱን እንዳይጥሱ የተለያዩ  ማስጠንቀቂያዎችና ትእዛዛቱን ከጣሱ ስለሚያገኛቸው ቅጣቶች ይናገራሉ። ከዚህ ሌላ ስላለፈው ዘመን፣ ስለመጪው ዘመን፣ ስለአዲስ ኪዳን፣ ስለ ክርስቶስ የሚናገሩት የትንቢት ክፍሎች አሉ። አብዛኛው የትንቢት ክፍል ይዘት ግን ከወቅቱ የእስራኤላውያን ሁኔታ ጋር የተያያዘ እና በአሁኑ ሰዓትም ፍጻሜን  ያገኘ ነው። የትንቢቶችን ይዘት በተናገሩባቸው ዘመናት ብንከፍላቸው እንደሚከተለው በሦስት ዘመናት ማየት ይቻላል።