Wednesday, October 16, 2013

አዲስ ኪዳን - የታሪክ ክፍል (የሐዋርያት ሥራ)

ባለፈው ክፍል በጀመርነው የአዲስ ኪዳን ዳሰሳ የወንጌል ክፍልን ማየታችን ይታወሳል። በዚህም ወንጌል ማለት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ ሕይወት ከልደት እስከ ሞትና ትንሣኤ በአራቱ ወንጌላውያን የተዘገበው የመጽሐፍ ቅዱስ የምሥራች ቃል መሆኑን ተመልከተናል። በመቀጠል ይህ ወንጌል በሐዋርያት በኩል እንዴት ወደ ዓለም መሰራጨት እንደጀመረ በአዲስ ኪዳን የታሪክ ክፍል በሚባለው በሐዋርያት ሥራ ተዘግቦ የምናገኘው ሲሆን ለዛሬ ይህን እናያለን።
የሐዋርያት ሥራ ስሙ እንደሚነግረን ሐዋርያት የሠሩት ወንጌል የማስፋፋት ሥራ ነው። ሐዋርያት በአንድነት መንፈስ ለአንድ የተቀደሰ ዓላማ በጽናት እንደሠሩ እናያለን። ይህ ኅብረታቸው ቤተ ክርስቲያን ይባላል። የቤተክርስቲያን ቀዳሚ ትርጉም የክርስቲያኖች ኅብረት /አንድነት/ ነው። መጽሐፉ በሐዋርያት የተመሠረተችው የመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን (ኅብረት) የነበራትን የአገልግሎት ትጋት ያሳየናል። የወንጌል ስብከትና መስፋፋት፣ ጸሎት፣ የጋራ የፍቅር ማዕድ (አጋፔ)፣ ሃብትና ንብረታቸውን በጋራ መጠቀም፣ የተቸገሩትን መርዳት፣ ድውያንን መፈወስ፣ የሥራ ክፍፍል /አስተዳደራዊ መዋቅር፣ በመሳሰሉት መንፈሳዊ አገልግሎቶች  እናያለን።
ከዚህም ጋር ከነበራቸው ጠንካራ አገልገሎት ጎን ለጎን ይደርስባቸው የነበሩ ፈተናዎች ነበሩ። ከአይሁድ የሚደርስባቸው ስደት፣ እንደ ሐናንያና ሰጲራ ካሉ ራስ ወዳዶች የሚመጣው ስስት፣ ከአይሁድ ጋር ስለነበራቸው የእምነት ግጭት፣ በውስጥ አስተዳደራዊና ቀኖናዊ ልዩነቶች ወዘተ የመሳሰሉ… ተግዳሮቶችን እንዳስተናገዱ ይታያል። ሐዋርያቱ ከፍተኛ የሆነ የወንጌል አገልግሎት ሥራ የሠሩት በከፍተኛ ተግዳሮት ውስጥ እያለፉ ስለነበር ምንጊዜም ዛሬም ከተሳካ አገልግሎት ጋር የከረረ ተቃውሞ የማይቀር መሆኑን እንገነዘባለን።