Monday, May 28, 2012

ጥያቄ ፭


በኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ ምዕራፍ ፮ ቁጥር ፮፡- እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ፥ በልቡም አዘነ። ይላል። እግዚአብሔር እንዴት ሰውን በመፍጠሩ ይጸጸታል። ይህ አባባል ምን ለማለት ነው?
መልሳችሁን/አስተያየታችሁን ከዚህ ጽሑፍ ሥር post comment  የሚለውን በመጫን መላክ ትችላላችሁ። 
መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት እንማማር፤ እንወያይ።

Monday, May 21, 2012

የአማርኛ ትርጉሞች ንጽጽር

Amharic Translations, read in pdf here

መጽሐፍ ቅዱስ በመጀመሪያ ከተጻፈባቸው እናት ቋንቋዎች በኋላ በዓለም ላይ ወደ ብዙ ቋንቋዎች ተተርጉሟል። በተመሳሳይ ቋንቋም ቢሆን ትርጉሙ በየጊዜው ይሻሻላል። ምክንያቱም በሥነ-ልሳን ትምህርት እንደሚታወቀው ቋንቋ ይወለዳል፤ ያድጋል፤ ይሞታል። ለምሳሌ የራሳችን የአማርኛ ቋንቋን ብንወስድ ከዛሬ 200 ዓመት በፊት የነበረው አማርኛ እና የአሁኑ አማርኛ በአነጋገርም፡ በአጻጻፍም ብዙ ልዩነቶች አሉት። ይህን በምሳሌ ለማስረዳት እስኪ ከማቴዎስ ወንጌል አንዱን ክፍል የተለያዩ የአማርኛ ትርጉሞችን እንይ።
የማቴዎስ ወንጌል ም ፯፣፩-፲፬  በልዩ ልዩ የአማርኛ ትርጉሞች፡
የቀድሞ ትርጉም የ1870ዎቹ፡
 አትፍረዱ፡ እንዳይፈረድባችሁ። በፈረዳችሁት ፍርድ ይፈረድባችኋልና፡ በምትሰፍሩበትም መስፈርያ ይሰፈርባችኋልና።
ለምንስ በወንድምህ ዓይን ያለውን ሰንጣቂ ታያለህ። ዓይንህም ያለውን መሰሶ አትመለከትም። እንዴትስ ወንድምህን ትለዋለህ፡ተወኝ ካይንህ ሰንጣቂ ላውጣልህ። እነሆ መሰሶም ዓይንህ ነው። አንተ ግብዝ አስቀድመህ መሰሶ ካይንህ አውጣ። ከዘያ በኋላም ታያለህ፡ ሰንጣቂውን ከወንድምህ ዓይን ታውጣ ዘንድ።
የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ፡ እንቆችሁንም አትጣሉ፡ በእርዮች ፊት፡ በግሮቻቸው እንዳይረግጡት ተመልሰውም እንዳይነክስዋችሁ።
ለምኑ ይሰጣችኋልም። እሹ ታገኙማላችሁ። ደጅ ምቱ ይከፈትላችኋልም። የለመነ ሁሉ ይወስዳልና። የፈለገም ያገኛል፡ ደጅም ለመታ ይከፈትለታል።
ወይስ ምን ሰው ከላንት ነው ልጁ እንጀራ ቢለምነው በውኑ ደንጊያ ይሰጠዋል። ዓሣስ ቢለምነው እባብን ይሰጠዋል። 

Sunday, May 13, 2012

ለቃሉ መታዘዝ

Lekalu Metazez, read in pdf here
ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችን በዋናነት የሚያስፈልጉንን እግዚአብሔርንና ክርስቶስን ማወቅ በምሥጢረ-ሥላሴና በምሥጢረ-ሥጋዌ ፣ እንዲሁም ጸሎት የሚሉትን ርእሶች ባለፉት ተከታታይ ትምህርታችን ማየታችን ይታወሳል።  ቀጣዩ ዋና አስፈላጊ ጉዳይ ለቃሉ መታዘዝ የሚለው ነው።
መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው፡ ለታሪክ፡ለምርምር፡ ለጠቅላላ ዕውቀት፡ ለግንዛቤ፡ ወይም ለመረጃ አይደለም። የተጻፈበት ቀዳሚ ዓላማ ለሕይወት ነው። ቃሉ በሁለት ወገን እንደተሳለ ሰይፍ ላመኑበት መዳንን ላላመኑት ደግሞ ፍርድን የሚያስከትል  እንዲሁም ተናጋሪውንም አድማጩንም የሚነካ ኃይል ያለው፡ እና የሚሰራ ነው። የመዳንንም ራስ ቁር የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው። ኤፌ ፮፡፲፯
የእግዚአብሔር ቃል ሕያው ነውና፥ የሚሠራም፥ ሁለትም አፍ ካለው ሰይፍ ሁሉ ይልቅ የተሳለ ነው፥ ነፍስንና መንፈስንም  ጅማትንና ቅልጥምንም እስኪለይ ድረስ ይወጋል፥ የልብንም ስሜትና አሳብ ይመረምራል፤ ዕብ ፬፡፲፪
መጽሐፍ ቅዱስን መታዘዝ አለብን ስንል መጽሐፉ ከዳር እስከ ዳር ይህን አድርግ ይህን አታድርግ በሚሉ ትእዛዛት የተሞላ መጽሐፍ ነው ማለታችን አይደለም። እግዚአብሔር እንድንታዘዘው የሚፈልገውን ሃሳብ በቃሉ ውስጥ በተለያየ መንገድ አስቀምጧል። ይህንንም ማስተዋል የኛ ድርሻ ይሆናል።
« እግዚአብሔር በአንድ መንገድ በሌላም ይናገራል ሰው ግን አያስተውለውም።» ኢዮ ፴፫፥፲፬፤
እግዚአብሔር ከሚያስተምርባቸው መንገዶች የሚከተሉት ዋናዎቹ ናቸው።