Friday, December 12, 2014

እኔ ማን ነኝ?


እኔ….. ነኝ ብሎ በሥልጣን ቃል የተናገረ፡
በብሉይ ኪዳን፡ እግዚአብሔር ብቻ፡ ነው።….ሰባቱን ብናይ፡-
-      እኔ ለአንተ ጋሻህ ነኝ። ዘፍ ፲፭፣፩
-      እኔ ኤልሻዳይ ነኝ።. ዘፍ ፲፯፣፩
-      የአባቶችህ አምላክ እግዚአብሔር እኔ ነኝ። ዘፍ ፵፮፣፫
-      ያለና የሚኖር እኔ ነኝ። ዘጸ ፫፣፲፬
-      እኔ እግዚአብሔር ነኝ። ዘጸ ፮፣፫
-      ከግብጽ ምድር ከባርነት ቤት ያወጣሁህ እግዚአብሔር አምላክህ አኔ ነኝ። ዘጸ ፳፣፪
-      እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ቀናተኛ አምላክ ነኝ። ዘጸ ፳፣፪
በአዲስ ኪዳን፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ፡ ነው።….ሰባቱን ብናይ፡-ለ
-      የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ። ዮሐ ፮፣፴፭
-      እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ። ዮሐ ፰፣፲፪
-      እኔ የበጎች በር ነኝ። ዮሐ ፲፣፯
-      መልካም እረኛ እኔ ነኝ። ዮሐ ፲፣፲፩
-      ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ። ዮሐ ፲፩፣፳፭
-      እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ። ዮሐ ፲፬፣፮
-      እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ። ዮሐ ፲፭፣፩
እኔ…..እንዲህ… ነኝ ብሎ የተናገረና መናገር የሚችል አምላክ ብቻ ነው። ምክንያቱም፡-
፩. የማይለወጥ /የማይወሰን ስለሆነ፡
እንዲህ / እዚህ ነበርኩ። እንዲያ / እዚያ እሆናለሁ… አይልም። ቦታ ጊዜ ሁኔታ አይገድበውም።
እግዚአብሔር አይለወጥም፡ አይወሰንም።
ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትና ዛሬም እስከለዘላለምም ያው ነው።… ዕብ ፲፫፣፰

፪. ሁሉ በእጁ / በእርሱ ስለሆነ፡
እግዚአብሔር ሁሉን ፈጥሮአል፣ ሁሉን ይመግባል።
ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን። ሮሜ ፲፩፣፴፮።
፫. ከእርሱ በላይ ማረጋገጫ ስለሌለ፡
አንድ ነገር -- ነው / አይደለም-- የሚል ልዩነት ቢፈጠር በሦስተኛ / በበላይ አካል እንዲረጋገጥ ይደረጋል።
እግዚአብሔር ሌላ አስረጅ፣ ምስክር አያስፈልገውም። ከእርሱ በላይ የሚያረጋግጥ ስለሌለ።
፬. ነኝ ያለው የሆነውን ስለሆነ
ሁልጊዜ የነበረውን፣ የሆነውን፣ ወደፊትም የሚሆነውን ነኝ አለ።
ያልሆነውን፣ የማይሆነውን ነኝ አላለም፤ አይልምም።

Wednesday, December 3, 2014

የፈቃዱ ምሥጢር - ክፍል ፪

......ባለፈው ክፍል ኤፌ ፩፣ ፩ - ፲፬
.... በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤
በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።...
የሚለውን አሳብ ማየታችን ይታወሳል። ከዚህ ክፍል ምን እንማራለን? 
፩. ምሥጢረ-ሥላሴ፡-
Ø  መዳናችን የሥላሴ ሥራ ነው ። ሥላሴ - አብ ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ።
²  አብ - ዓለም ሳይፈጠር - አቀደ -- የአሳብ መነሻ - ልብ።
²  ወልድ - ዓለም ከተፈጠረ በኋላ - ሰው ሆኖ የአብን ዕቅድ ፈጸመ፣ ሞቶ አዳነን።
²  መንፈስ ቅዱስ - ዓለም ካለፈ በኋላ ለምንወርሳት መንግሥተ ሰማያት አሁን ማረጋገጫ /ማኅተም ሆነ።
፪. ምሥጢረ ሥጋዌ    
Ø  ቁ. ፫፡- የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት
²  አምላክ -ሲል- ክርስቶስ ፍጹም ሰው መሆኑን
²  አባት - ሲል- ክርስቶስ ፍጹም አምላክ መሆኑን - የአብ የባሕርይ ልጅ መሆኑን ያሳያል።
፫. ሁሉ በክርስቶስ እንደሆነና እንደሚሆን -  ሁሉ በእርሲ ሆነ ዮሐ ፩፣ ፫።
-      ከቁ .፩ - ፲፬ -- ኢየሱስ ክርስቶስ  ፲፬ ጊዜ ተጠቅሷል። -- በየቁጥሩ ማለት ይቻላል። ቃሎቹን ብናያቸው፡-
Ø  የኢየሱስ ክርስቶስ  ፩  ፫ 
Ø  በክርስቶስ ኢየሱስ  ፩ 
Ø  ከኢየሱስ ክርስቶስ  ፪  --- ምንጭን ያሳያል - የጸጋና የሰላም ምንጫችን እርሱ ነው።
Ø  በኢየሱስ ክርስቶስ  ፭
Ø  በውድ ልጁ  ፮  ፯
Ø  በክርስቶስ ፫  ፬  ፱  ፲  ፲፩  ፲፪  ፲፫
-      የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ - ባለቤትነቱን ያሳያል። እንደ ሐዋርያ ሆኖ የሚሠራ ማንኛውም አገልጋይ የኢየሱስ ክርስቶስ ነው። - የእገሌ ወይም የቤተ ክርስቲያን አይደለም።
Ø  ራሱን ያስተዋወቀበት ስም ነው።-  ክርስቶስ መታወቂያው ሆነ ፤ መታወቂያችን ሊሆን ይገባል።
-      ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም - ምንጭን ያሳያል። የተደረገልን የመዳን ጸጋ/ቸርነት እና ያገኘነው ሰላም ምንጩ ክርስቶስ ነው።

Friday, November 28, 2014

የፈቃዱ ምሥጢር - ክፍል ፩


በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ፥ የፈቃዱን ምሥጢር አስታውቆናልና፤
በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ በክርስቶስ ለመጠቅለል ነው።
ኤፌ ፩፣ ፱ - ፲  / ሙሉ ሃሳቡ ከቁ ፩ - ፲፬፤/
ፈቃዱ፡- ፍላጎቱ፣ አሳቡ፣ እቅዱ፣ ዓላማው፣ ውሳኔው ማለት ነው።
ምሥጢር፡- የማይነገር ስለሆነ ሳይሆን ተሰውሮ የኖረ በኋላ የተገለጠ ለማለት ነው።
ይህም የእግዚአብሔር የዘላለም ሃሳብ የሆነ መለኮታዊ ዕቅድ ነው።
-      ከቁ. ፫ - ፲፬፡- በግሪኩ አንድ ረጅም አረፍተ ነገር ነው፡፡ እኛም በአንድ አረፍተ ነገር ብናጠቃለው፡-
Ø  «እግዚአብሔር በክርስቶስ ለሆኑት ልጆቹ ስላደረገው መንፈሳዊ በረከት ክብር ምስጋና ይገባዋል።»  የሚል ይሆናል።
፩. ራሱን ማስተዋወቅ፡-  - የድሮ ደብዳቤዎች ሲጀምሩ ጸሐፊው ራሱን በመጥቀስ ነው።  
 ጳውሎስ ሐዋርያ የሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው።
ከ፲፪ቱ ሐዋርያት ጋር አልተጠራም፤ በኋላ በክርስቶስ መገለጥ በልዩ አጠራር ተጠራ።
የመልዕክቱ አድራሻ፡- በኤፌሶን ላሉት፣ በክርስቶስ ላሉት - አሁንም ለእኛ፡፡ - ተዘዋዋሪ ደብዳቤ ነው ይሉታል።
፪. ሠላምታ፣-  ጸጋና ሠላም - የጳውሎስ የተለመደ ሰላምታ።
ጸጋ፡- እግዚአብሔር መዳናችንን የሰጠበት የራሱ ነጻ ስጦታ። ቸርነቱ አይለየን፤ ጤና ይስጥልን እንደማለት ነው፡
ሠላም፡- ከዳንን በኋላ በክርስቶስ የሚኖረን እረፍት -- ሠላም ለናንተ ይሁን።
፫. በረከት፡- በረከት፣ የባረከን፣ ይባረክ።  ይህ በረከት፡-
Ø  በክርስቶስ የተደረገ ነው፤ ምክንያቱም መርገም በሰይጣን መጥቶ ነበርና ፡በአዳምና በልጆቹ ዘፍ ፫ና ፬
Ø  ሰማያዊ ነው። - ምድራዊ አይደለም፡- ቀዳሚው ነገር ነው።
Ø  መንፈሳዊ ነው። - ሥጋዊ / ቁሳዊ አይደለም።
Ø  ዘላለማዊ ነው፡፡ - ጊዜያዊ አይደለም።
²  የሚቀድም፣ የማይቀር፣ ዘላለማዊ በረከት ነው - የተፈጠርንበት ዋና ዓላማ።

Tuesday, November 18, 2014

የሰናፍጭ ቅንጣት - ክፍል ፪

1.     ከምሳሌው ምን እንማራለን?
1.     የሰናፍጭ ዘር --- ወደ ዛፍነት ያድጋል
Ø  ከሁሉ ያነሰና ከግምት የማይገባ ጥቂት ጅማሬ -- ወደ ታላቅ ግብ ይደርሳል።
Ø  ከቅንጣት - የጎላ ዕድገት ይወጣል
² በሥጋዊ አካል ስናየው የወንድ ዘር በዓይን የማይታይ ረቂቅ ነው፤ የሴትም እንቁላል በጣም ትንሽ ናት። ከእነዚህ ውህደት ጽንሱ ሲፈጠር በእጅ ጭብጥ አይሞላም።
² ከዚህ ውስጥ ግን የተለያየ አካል ይወጣል። ያድጋል። -- በመንፈሳዊውም እንዲሁ ነው።
Ø  የእግዚአብሔር መንግሥትም እንዲሁ ነው።
ክርስቶስ መንግሥቱን ለመመስረት በዚች ምድር ሲወለድ - የተናቀ፣ የተሰደደ፣ ብቻውን ነበረ።
በኋላ 12 ሐዋርያትን -ቀጥሎ- 120 ቤተሰብ -ከዚያ- 3ሺ-- 5ሺ --እያለ ዛሬ ክርስትና በመላው ዓለም ተስፋፋ። ወደፊትም ይቀጥላል።
²  የቤተክርስቲያን /የክርስቲያኖች/ እድገት እንዲሁ ነው።
2.    የሚያድገው መጀመሪያ በመሞት ነው።
Ø  ዘሩ ወደ መሬት ወደቆ - ይሞታል - በኋላ ይነሳል። -- እንደ ክርስቶስ ትንሣኤ
አንተ ሞኝ፥ አንተ የምትዘራው ካልሞተ ሕያው አይሆንም፤
የምትዘራውም፥ ስንዴ ቢሆን ከሌላም ዓይነት የአንዱ ቢሆን፥ ቅንጣት ብቻ ነው እንጂ የምትዘራው የሚሆነውን አካል አይደለም፤
እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አካልን ይሰጠዋል ከዘሮችም ለእያንዳንዱ የገዛ አካሉን ይሰጠዋል።
፩ ቆሮ ፲፭፣ ፴፮ - ፴፰።
Ø  የእግዚአብሔር ሰማያዊ መንግሥት - በምድር - በክርስቶስ ሞት እና ትንሣኤ ተመሠረተ። ሰዎች የዘላለም ሕይወት /መንግሥተ ሰማያት የሚወርሱት ሞቱንና ትንሣኤውን ሲያምኑ ነው።
Ø  ይህንን የሕይወት የእግዚአብሔር መንግሥት ጥሪ ከአገልጋዮች እንደተቀበልነው እኛም ለሌላውም ማስተላለፍ አለብን።
Ø  ለማደግ- መውረድ፣ ከፍ ለማለት -ዝቅ ማለት የክርስትናው መሠረታዊ መመሪያ ነው።
Ø  ለሌሎች ለመትረፍ፣ ሌሎችን ለማዳን በቅድሚያ ለእኔነት መሞት ያስፈልጋል።
ክርስቶስ በኖረበት ዘመን ሁሉ የእኔ የሚለው አልነበረውም። ለእኔም አላለም።
አንድ መምህር እንዳለው፣ -« ክርስቶስ መለኮታዊ ኃይሉን ሌሎችን ለመርዳት እንጂ ራሱን ለማዳን አንድ ጊዜም አልተጠቀመም።»
Ø  ስለዚህ - ለእኔ - ከሚለው በፊት ለወገኔ - የሚለው ከቀደመ- ወንጌሉ / መንግሥቱ ይስፋፋል፤ - ትርፉ እንኳን በመንፈሳዊ - በሥጋዊም ጭምር ነው። መልካምነትም ይበዛል፤ ችግረኞችን አናይም፤
3.   በአደገች ጊዜ -- ራሷን ትችላለች

Wednesday, November 12, 2014

የሰናፍጭ ቅንጣት ክፍል ፩


ሌላ ምሳሌ አቀረበላቸው እንዲህም አለ፦ መንግሥተ ሰማያት ሰው ወስዶ በእርሻው የዘራትን የሰናፍጭ ቅንጣት ትመስላለች፤
እርስዋም ከዘር ሁሉ ታንሳለች፥ በአደገች ጊዜ ግን፥ ከአታክልቶች ትበልጣለች የሰማይም ወፎች መጥተው በቅርንጫፎችዋ እስኪሰፍሩ ድረስ ዛፍ ትሆናለች።   ----  ማቴ 13፣ 31-32/
-      ጌታችን ስለመንግሥቱ በምሳሌ አስተማረ - ለምን?
Ø  ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን በምሳሌ እንደሚያስተምር ተጠይቆ የመለሰው ምክንያት፡-
²  ደቀ መዛሙርቱም ቀርበው። ስለ ምን በምሳሌ ትነግራቸዋለህ? አሉት።
እርሱም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ ለእናንተ የመንግሥተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል፥ ለእነርሱ ግን አልተሰጣቸውም።
ላለው ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል።
ስለዚህ እያዩ ስለማያዩ እየሰሙም ስለማይሰሙ ስለማያስተውሉም በምሳሌ እነግራቸዋለሁ።
ማቴ 13፣ 10 – 13።
²  ሐዋርያት በክርስቶስ አምነው የእግዚአብሔር ልጆች ስለሚሆኑ - ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቷችኋል አላቸው።
²  ለሌሎች ግን ገና በኃጢአት፣ በጨለማ ውስጥ ስላሉ የመንግሥቱን ነገር ማወቅ አይችሉም።
Ø  የዕውቀት ውስንነት - በኃጢአት/ በውድቀት ከነበሩን ሦስት የነፍስ መልኮች ፣ ዕውቀት፣ ቅድስና እና ጽድቅ -- እውቀታችን ጎደለ። - ይህን ክፍተት ለመሙላት - ምሳሌ አስፈለገ።
Ø  የስሜት ውስንነት- በውስን ተፈጥሯችን፣ በአምስቱ የስሜት ሕዋሳት የማንገነዘባቸው ብዙ ነገሮች አሉ። ስለዚህ በምናያቸው ነገሮች መግለጽ የግድ ነው።
Ø  ምሳሌው የእኛን ደካማነት ብቻ ሳይሆን - የእርሱን ጥበበኛነት ያሳያል። ጥበበኛ መምህር ነው።  
-      አባቶች ምሳሌ ዘየሐጽጽ ይላሉ።- ምሳሌ - ከሚመሰልለት ነገር ያንሳል፣ በማነሱ ግን ትልቅ ነገርን ያብራራል፧
-      ዓለምን/ ምድራችንን በሉል - መስለን እንማራለን፡፡
-      ጥበብሰ መድኃኒነ ውእቱ እንደተባለው በቅዳሴ ጥበብ የተባለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወሰን የሌለውን እጅግ ታላቅ የሆነውን መንግሥተ-ሰማያት፣ -መጠን በሌላት -እጅግ ታናሽ በሆነች- በሰናፍጭ ቅንጣት -መስሎ አስተማረ። የሚገርም ምሳሌ ነው።
-      የእግዚአብሔር መንግሥት በሰናፍጭ ቅንጣት የተመሰለችው በዚህ ዓለም ሳለች ነው። ጅማሬዋ ነው። ፍጻሜዋ ግን በሰማይ ነው። ሩቅ አና ረቂቅ ነው።
-      የሰዎች መንግሥት በኃያልነት፣ በታላቅነት ሊገለጽ ይችላል።
Ø  የድሮ መንግሥታት / ነገሥታት ኃያልነት የሚታወቀው በግዛታቸው ስፋት… መሬት /ቅኝ ግዛት በማስፋፋት ነው።
²  የዓለም ጦርነቶች የተካሄዱት በአብዛኛው በድንበር ግጭት እና ከቅኝ ግዛት ነጻ ለመውጣት ነው።
Ø  የዚህ ዘመን መንግሥታት -- የአሜሪካ መንግሥት፣ የእንግሊዝ መንግሥት -- ኃያላን ሃገራት - የተባበሩት መንግሥታት… በጦር ኃይላቸው፣ በኢኮኖሚያቸው፣ ወዘተ.. ኃያልነታቸውን ይገልጻሉ።
²  እነዚህ ሁሉ የፈለገ ኃያላን ቢሆኑ - ይወድቃሉ፣ ያልፋሉ። - ከዚህ ቀደም የነበሩ ኃያላን መንግሥታት አልፈዋል።
Ø  የእግዚአብሔር መንግሥት ግን በዚች ምድር - እዚህ ግባ በማትባል - በአንዲት ዛፍ - ፍሬ- ዘር - በሰናፍጭ ቅንጣት- ተመስላለች። -
²  ስትጀመር / ስትመሠረት መሬት ወድቃ የምትጠፋ / የጠፋች/ ትመስላለች። ግን ትወጣለች ታድጋለች። -- የሚገድባትም የለም።
²  በአንዱ በክርስቶስ ሞት የተመሠረተው የእግዚአብሔር መንግሥት ለዓለም እና ለዘላለም ስለሚቀጥል እስከዛሬ በመላው ዓለም ተስፋፍቷል፣ በሰማይም ለዘላለም ይቀጥላል።
Ø  የሰዎች / አገሮች መንግሥታት የሚመሰረቱት - በኃይል እና በጦርነት--- በመግደል ነው። ስለዚህ መስራቾቹ ይገድላሉ - በኋላ ግን እነርሱ ይሞታሉ። መንግሥታቸው በሌላ መንግሥት ይተካል።
በታሪክ እንደታየው ብዙ ጊዜ የመንግሥት ለውጥ የሚደረገው በኃይል እና በጦርነት ነው።
Ø  የእግዚአብሔር መንግሥት ግን የተመሠረተችው በመሞት ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ በመሞት ተከታዮቹም ይሞታሉ - በኋላ ግን ክርስቶስ እንደተነሳ ሕያው ይሆናሉ።
-      ዛፍ የመንግሥት ምሳሌ ሆኖ የቀረበው በዳንኤል ዘመን ለንጉሡ ለናቡከደነጾር መንግሥት ነው። /በሕልም/
Ø  …..ቅጠሉም አምሮ የነበረው፥ ፍሬውም የበዛው፥ ለሁሉም መብል የነበረበት በበታቹም የምድር አራዊት የተቀመጡ፥ በቅርንጫፎቹም የሰማይ ወፎች ያደሩበት ያየኸው ዛፍ - ንጉሥ ሆይ፥ እርሱ ታላቅና ብርቱ የሆንህ አንተ ነህ ታላቅነትህ በዝቶአል፥ እስከ ሰማይም ደርሶአል፥ ግዛትህም እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ነው።   ዳን 4፣ 10 – 12 ፡ 20 -22።
1.     የምሳሌው አስፈላጊነት
-      ሰይጣን የእግዚአብሔርን ቃል መሰራጨት እና የወንጌሉን መስፋፋት ይቃወማል። ከምሳሌዎች ዝርዝር ከላይ በእርሻው መካከል እንክርዳድ እየዘራ እንደሚቃወም። ማቴ 13፣24 - 28
ይህ ከሆነ የእግዚአብሔር መንግሥት እንዴት ይስፋፋል? የሚለውን ለማብራራት ነው።
2.    የዘሩ / የዛፉ ጠባይ / Biological Characters/
-      የሰናፍጭ - -ቅንጣት -- በምድር ካለ ዘር ሁሉ ታንሳለች። - በመጠንም ፣ በክብደትም።
Ø   በመጠኑ፡- (ስፋት..) - ሊለኩ ከሚችሉ ነገሮች ሁሉ እጅግ ያነሰ
²  ክብደቱ - ሊመዘኑ ከሚችሉ ነገሮች ሁሉ እጅግ የቀለለ
Ø  የጎመን ዘር ዓይነት ሆኖ ፍሬው በጣም ትንሽ ነው።፣  - በነፍሳት በቀላሉ የማይጠቃ።
Ø  በብዙ ዓይነት አፈር በቀላሉ ሊበቅል የሚችል፣ ከፍተኛ የአየር ንብረት ለውጥ የሚቋቋም።
Ø  ፍሬው ውስጥ ያለው ዘሩ በጣም ደቃቅ ሲሆን የዛፉ ቁመት ግን ረጅም ነው፡
እንደዘሩ ዓይነት፣ እንደአፈሩ እና አየሩ ሁኔታ በአንድ ዓመት ከ4 – 10 ሜትር ያድጋል።
Ø  አእዋፍ እስኪሰፍሩበት ድረስ -- ሌሎችን እስኪሸከም ድረስ ያድጋል። ይጠነክራል።
ከምሳሌው ምን እንማራለን?
 ---------ይቀጥላል
----ይቆየን፤

Saturday, November 8, 2014

ስለጉድለት አልልም - ፪

.......ሰይጣን በጉድለታችን ይፈትነናል። እግዚአብሔር ይህን እያወቀ ለምን ዝም ይላል?
፫. ጉድለታችን ለእግዚአብሔር ምን ያደርግለታል?
እግዚአብሔር ጉድለታችንን ያውቃል። ጉድለታችን፡-
1.     የእርሱ ሙላት መገለጫ
-      የእስራኤልን ሕዝብ ግማሽ ሚሊየን በላይ የመራው ሙሴ ኮልታፋ ሰው ነበረ።
ዘጸ ፬፣፩-፲፫። ሙሴ እግዚአብሔርን ሌላ ሰው ፈልግ፡ ብሎት ነበረ።
-      ከመወለዱ ጀምሮ አይነ ስውር ሆኖ የተወለደው ሰው በማን ኃጢአት እንደዛ ሆነ?
ዮሐ ፱፣፩-፫። …«የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ እንዲገለጥ ነው። »
የእስራኤል ተወዳጅ ንጉሥ ዳዊት እረኛ የተናቀ.. ለንግሥና ምርጫ የተረሳ ነበረ።
እግዚአብሔር በተናቁ፡ ጉድለት በሚታይባቸው ፣ በጉድለታችን መሥራት ልማዱ ነው።
ክብሩን ለመግለጽ።
ሙላታችን አያግዘውም። ጉድለታችን አያደናቅፈውም። ብቻውን ይሠራል…ብቻውን ክብሩን ይወስዳል።
2.    እርሱ ብቻ እንዲመለክ፡
አዳም አንዲት ዛፍ የከለከለው እግዚአብሔርን እንዳይረሳ/ እንዲያስታውስ ነው።
ሁሉ ነገር ቢሰጠውና ቢፈቀድለት እኔ ከሁሉ በላይ ነኝ ብሎ በትዕቢት እንደሳጥናኤል እንዳይወድቅ።…
-      ሁሉ ነገር ቢሟላልን እግዚአብሔር ይረሳል።
-      ሁሉ ነገር ቢጎድል መኖር አይቻልም።
ስለዚህ እግዚአብሔር ሆን ብሎ ሕይወትን በጉድለት አዋቀራት።
«ጎደሎው የጸሎት ርእስ ነው።» ይባላል። ካለዚያ አምላክን እንረሳለን።
3.    ለኛ ጥቅም ነው።
ከተሰጡን ነገሮች ጋር አንድ አንድ ጉድለት አለ። በዚች ዓለም ፍጹም የሆነ ነገር የለም።
ሰዎች ስንባል ለመያዝ (ያ - ይጠብቃል) የምናስቸግር ፍጡሮች ነን።
እስራኤላውያንን ከግብጽ በታላቅ ተአምራት አውጥቶ በበረሃ መና እየመገበ ሲመራቸው መና ሰለቸን አሉ።  ዘኁ ፲፩፣ ፮
ምድረ ርስትን ለመውረስ ተዘጋጅተው በነዋሪዎቹ ሃያልነት ወሬ በግብጽ ምነው በሞትን አሉ?.... ዘኁ ፲፫ ና ፲፬
ብዙ ጊዜ ችግራችን የተደረገልንን እንረሳለን። እንለወጣለን።….
-      ለመያዝ (ያ - ይጠብቃል) የሚያስቸግሩ ዕቃዎች ማንጠልጠያ ቀዳዳዎች አሉአቸው።
ለትኩስ ሻይ በብርጭቆ ማንጠልጠያ፣ ለጋለ ብረት ምጣድ ጆሮ… አሉአቸው።
መያዣዎቹ ቀዳዳዎች.. ክፍተቶች ናቸው።… ጉድለቶች።
-      እኛም ጉድለቶቻችን መያዣዎቻችን (ያ - ይጠብቃል) ናቸው። እግዚአብሔር እኛን የሚይዝበት።
-      በምድር ሁሉ ቢሞላልንና ፍጹም ሰላምና እረፍት ቢሆን የመንግሥተ ሰማያት ጉዞአችንን እናቆማለን። እንረሳለን። አንድ ወንድም እንዳለው፡-
 ለእግዚአብሔር፡ « በቃ፡ መንግሥተ ሰማያት ምና ምን የምትለውን ተወው. እዚሁ ተመችቶኛል… » እንዳንል።
፫. በተስፋ እንድንኖር  በምድር በመጨረሻም እስከ ሰማይ።
ሕይወት ቀጣይ የምትሆነው በጉድለት ስለተዋቀረች ነው።
ዛሬ ጥረት የምናደርገው ዛሬ የሌለንን ነገር ነገ ለማግኘት ነው።
ዛሬ የምንማረው ነገ ሥራ ለመያዝ ነው።.. ስንይዘውም ከዚያ የተሻለ ሥራ እንፈልጋለን…..
ዛሬ ሥራ ስንይዝ ትዳር እናስባለን።… ትዳር ሲመጣ ልጅ እናስባለን።……
አንዱ ሲሞላ.. ሌላ ጉድለት። ያ ሲሞላ… ሌላ ጉድለት… እያለ ኑሮ ይገፋል።  እስከ ሞት።
-      የዛሬ ጉድለት የሁልጊዜ ጉድለት አይደለም / አይሆንምም።
-      ጉድለት ይሞላል፡ ግን አብሮ ሌላ ጉድለት ይዞ ይመጣል።
የዚች ዓለም መዋቅር እነደዚህ ነው። ከጨለማ ቀጥሎ ብርሃን። ከብርሃን ቀጥሎ ጨለማ።
ጨለማው እንደጨለመ አይቀጥልም።… ይነጋል።
ብርሃኑም እንደበራ አይኖርም። … ይመሻል።
ጨለማው ጉድለታችን የሚያማርረን ሊሆን አይገባም።
ብርሃኑ ሙላታችንም የሚያስጨፍረን አይደለም።
ስለዚህ ሁሉም በልክ ይሁን።
የማያቋርጥ ፍጹም ሰላምና እረፍት በመንግሥተ ሰማያት ብቻ ነው።
ጉድለታችን የዚች ዓለም መኖሪያና መያዣችን የሆነ አምላካዊ ጥበብ ነው።

በጉድለታችን ውስጥ በእግዚአብሔር ደስ ሊለን ይገባል።