Tuesday, March 27, 2012

የጥያቄ ፬ መልስ (ቀጣይ)


Proof Bible is word of God p 2, read in pdf
መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ለመሆኑ የሚያስረዱትን ውስጣዊ ማረጋገጫና ከውጫዊ ማረጋገጫዎች የመጀመሪያውን የመጽሐፍ ቅዱስን ተከታታይነትና ወጥነት ባለፈው አይተን ቀሪውን በዚህ ክፍል እናያለን።


ለ. የመጽሐፍ ቅዱሳዊ መገለጥ ጥልቅነት፡- እውነትን በመግለጥ ረገድ መጽሐፍ ቅዱስ ተመርምሮ አያልቅም። ቴሌስኮፕ የሰማይን ከፍታ እንደሚያሳይ፡ መጽሐፍ ቅዱስም የእግዚአብሔርን የእጅ ሥራዎች ከመነሻ እስከ ፍጻሜ፡ ከሰማይ ከፍታ እስከ ሲኦል ጥልቀት ያመለክታል። ማይክሮስኮፕ ረቂቅ ነገሮችን እንደሚያሳይ ሁሉ ረቂቁ የእግዚብሔር፥ ሥራ ዕቅድና ዓላማው እንዲሁም የፍጥረቱ ፍጹምነት በመጽሐፍ ቅዱስ ተገልጧል። ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተካተቱት ብዙ መጻሕፍት የተጻፉት ጸሐፊዎቹ ስለዘመናዊው ግኝት ግምት ባልነበራቸው ጊዜና በጥንታዊው የሰው ልጅ እውቀት ደረጃ ቢሆን፡ በቅርቡ የተገኙት የሥነ-ምድር ምርምር ጥናቶች መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉትን እውነቶች ከመቃረን ይልቅ ይደግፋሉ። ጥንታዊዎቹ ቅዱሳት መጻሕፍት በሚያስደንቅ አኳኋን ከዘመናዊው የሥነ-ምድር ምርምር ግኝቶች ጋር ይስማማሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ዘላለማዊነት ያላቸውንና በእግዚአብሔር ብቻ የሚታወቁትን እውነቶች ስለሚገልጥ፥ ከሰው ምርምርና ግኝት በላይ የሆኑ እውነቶችን ይዟል። መጽሐፍ ቅዱስ እውነትን በሙላትና በረቂቅነት የሚያሳየንን ያህል የሚያሳይ ሌላ መጽሐፍ በዓለም የለም።

ሐ. የመጽሐፍ ቅዱስ የመለወጥ ኃይልና ኅትመቱ፡ በዓለማችን የመጽሐፍ ቅዱስን ያህል ለተለያዩ ሕዝቦችና ባሕሎች በተለያዩ አያሌ ቋንቋዎች የታተመ ሌላ መጽሐፍ የለም። የማተሚያ መኪና እንደተፈለሰፈም ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመው መጽሐፍ ቅዱስ ነው። በዓለም ታላላቅ ቋንቋዎች ሁሉ በብዙ ሚሊየን ቅጂዎች ታትሟል። ጽሑፍ ያለው እያንዳንዱ ቋንቋ ከመጽሐፍ ቅዱስ ቢያንስ ጥቂት ክፍሎች የታተመ ነገር አለው። ምንም እንኳን እንደ ፈረንሳዊው ቮልቴር ያሉ ሃይማኖት የለሾች መጽሐፍ ቅዱስ ከአንድ ትውልድ ዕድሜ በኋላ ከአገልግሎት ውጪ ይሆናል ቢሉም፥ የሀያኛው ክፍለ-ዘመን ደራሲያንም መጽሐፉ ይረሳል ወይም ፈላጊ አይኖረውም ቢሉም፥ ካለፈው ይበልጥ በብዙ ቋንቋዎች በመታተም ላይ ነው። በተከታዮች ብዛት ከክርስትና የሚበልጡ ሌሎች ሃይማኖቶች ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ሊወዳደር የሚችልና መገለጥ ያለው ጽሑፍ ሊያቀርቡ አልቻሉም። የመጽሐፍ ቅዱስ ሕይወትን የመለወጥ ኃይል በዘመናችንም ቀጥሏል።

Wednesday, March 21, 2012

የጥያቄ ፬ መልስ (ክፍል ፩)


4. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ለመሆኑ ማረጋገጫው ምንድን ነው?
 Proof the Bible is Word of God part-1,READ IN PDF

መጽሐፍ ቅዱስ የሰውን ልጅ የብዙ ዓመታት ታሪክ የሚያጠቃልል ሲሆን ከአርባ በሚበልጡ በተለያዩ ዘመናትና ሁኔታዎች ውስጥ ባለፉ ሰዎች የተጻፈ ነው። ይሁን እንጂ የማይገናኙ ልዩ ልዩ ጽሑፎች ስብስብ ሳይሆን አስደናቂ ተከታታይነትና ወጥነት ያለው መጽሐፍ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን የሚደግፉ ሁለት ማረጋገጫዎች አሉ።  ፩. አንዱ ውስጣዊ ማረጋገጫ ነው። ይኸውም መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተመለከቱት እውነታዎችና መጽሐፉ ራሱ ስለመለኮታዊነቱ የሚገልጠው ሲሆን፣  ፪. ውጫዊ ማረጋገጫ ደግሞ ልዐለ-ተፈጥሮ የሆነውን ባሕርይውን የሚገልጹ ውስጡ የተጠቀሱት እውነቶች ናቸው።

፩. ውስጣዊ ማረጋገጫ፡-
 መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን በመቶ በሚቆጠሩ የንባብ ክፍል ራሱ አረጋግጦአል። የብሉይ ኪዳንና የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ክርስቶስም ጭምር መጽሐፍ ቅዱስ በእግዚአብሔር ገላጭነት የተጻፈ ነው ይላሉ።
  «ስለዚህ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ይህን እንደ ተናገረ አሰቡና መጽሐፍንና ኢየሱስ የተናገረውን ቃል አመኑ።» ዮሐ ፪፡፳፪
« ስለዚህም የመልእክትን ቃል እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ከእኛ በተቀበላችሁ ጊዜ፥ በእውነት እንዳለ በእናንተ በምታምኑ ደግሞ እንደሚሠራ እንደ እግዚአብሔር ቃል እንጂ እንደ ሰው ቃል አድርጋችሁ ስላልተቀበላችሁት፥ እኛ ደግሞ እግዚአብሔርን ሳናቋርጥ እናመሰግናለን።»  ፩ተሰ ፪፡፲፫።