Wednesday, September 26, 2012

ብርሃን ይሁን፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር የመጀመሪያው ቃል (ንግግር)
Birhan Yihun, sebket, READ IN PDF
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ ብርሃንም ሆነ። ዘፍ ፩፡፫
በመጽሐፍ ቅዱሳችን በመጀመሪያው መጽሐፍ በመጀመሪያው ምዕራፍ እግዚአብሔር በመጀመሪያ የተናገረው ቃል ብርሃን ይሁን የሚል ነው። ከዚያ በፊት ባሉት ቁጥሮች በዝምታ (በአርምሞ) ሲሠራ ቆይቷል። ሰማይ፡ ምድር፡ ጨለማ፡ መላእክት…. የተፈጠሩት በዝምታው ነው። እግዚአብሔር በዝምታውም ይሠራል። በኀልዮ ይላሉ፡፡ ሲያስብ ይፈጸማል፡ ይከናወናል። የሰው ሃሳብ ምናባዊ የሆኑ ብዙ ነገሮችን ሊያወጣ ሊያወርድ ይችላል። እግዚአብሔር ግን በሃሳቡ ብቻ ተጨባጭ ነገሮችን ያስገኛል።  ታላላቆቹና የፍጥረታት መሠረታውያን የተባሉት ፬ቱ ባሕርያት እሳት፡ ነፋስ፡ ውኃ፡መሬት የተፈጠሩት በኀልዮ፡ (በዝምታ) ነው።
እግዚአብሔር በምን ተናገረ?
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ። እግዚአብሔርም… አለ። ይህ የተናገረበት ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነው አካላዊ ቃል ወልድ በኋላም ሰው የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። እግዚአብሔር በሦስትነቱ ሥላሴ ሲባል አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው። ሥላሴ በአብ ልብነት ያስባሉ፡ በወልድ ቃልነት ይናገራሉ፡ በመንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሕያው ሆነው ይኖራሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር ዓለምን ሲፈጥር የተናገረበት ቃል ወልድ ነበረ።
በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ዮሐ ፩፡ ፩።
ያ ቃል ወልድ በሐዲስ ኪዳን ሥጋን ለብሶ ሰው የሆነው፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው፡ ዓለምን ሁሉ ያዳነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።  ….. ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ዮሐ ፩፡ ፲፬።

ዛሬ እግዚአብሔር በምን ይናገራል?  
- በብሉይ ኪዳን በዝምታ፡ በሕልም፡ በራእይ፡ በነቢያት፡…. በወልድ ቃልነት ይናገር ነበር።
ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ዕብ ፩፡፩
-በሐዲስ ኪዳን የሚያናግርበት መንገድ አንድ ብቻ ነው።
ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን።  ዕብ ፩፡፪
እንግዲህ እግዚአብሔር ዛሬ እኛን የሚያናግረን በዚያው ቃል - በወልድ - በኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህንም የምናውቀው በተጻፈው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ እና በመምህራን አማካይነት ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር የሚያናግረንን ለማወቅ፡ ብሎም ለመታዘዝ ቃሉን - ይሄውም ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን እና መጽሐፍ ቅዱስን - ማወቅ አለብን ማለት ነው። ይህ ቃሉ ዓለምን የፈጠረ - ፈጣሪ፡ ዓለምንም ያዳነ - አዳኝ ዛሬም የእኛን ሐይወት ያዳነ- የሚሠራ አካላዊ ቃል ነው። እግዚአብሔር ሲያናግረን ልናዳምጥና ልንጠቀምበት ይገባል።

Monday, September 17, 2012

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካዊ ዳሰሳ - አዲስ ኪዳን


ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችን አጠቃላይ ግንዛቤ ይረዳን ዘንድ በሁለቱ ኪዳናት ያሉትን ታሪኮች ጠቅለል አድርገን ለማየት የብሉይ ኪዳንን ታሪካዊ ፍሰት ባለፈው ትምህርታችን ማየታችን ይታወሳል። ለዛሬ የአዲስ ኪዳንን አጠቃላይ ይዘት እንዲሁ እንመለከታለን።
አዲስ ኪዳንን አዲስ ያሰኘው ብሉይ ኪዳን ያለፈ፣ ያረጀ ወይም የቆየ ስለሆነ ነው። ብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ጋር የገባው ቃል ኪዳን ሲሆን በእነርሱ አለመታዘዝ ምክንያት ኪዳኑ ሊጸኛ አልቻለም።
«ፊተኛው ኪዳን ነቀፋ ባይኖረው፥ ለሁለተኛው ስፍራ ባልተፈለገም ነበር።…. አዲስ በማለቱ ፊተኛውን አስረጅቶአል፤ »  ዕብ ፯፣ ፯ና ፲፫።
እስራኤላውያን እንታዘዛለን ብለው ቃል የገቡበትን ሕግ ሊያከብሩ ባለመቻላቸውና ሕጉን በመጣሳቸው እግዚአብሔር በዚያው በብሉይ ኪዳን ዘመን ሌላ አዲስ ኪዳን እንደሚመሠርት መናገሩን ካሁን ቀደም ጠቅሰን መማማራችን ይታወሳል። ዘጸ ፳፬፣፯።
« እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር፦ ኤር ፴፩ ፣ ፴፩ - ፴፬
አዲስ ኪዳን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን መላውን ዓለም /የሰው ዘር የሚመለከት እግዚአብሔር በልጁ ሞት ለሰው ያደረገው የቸርነቱን ሥራ የሚያሳይ ኪዳን ነው።
እንዲሁም ከእራት በኋላ ጽዋውን አንሥቶ እንዲህ አለ፦ ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው። ሉቃ ፳፪፣፳።
ካሁን ቀደም እንዳየነው ብሉይ ኪዳን ስለአንድ ሕዝብ - ስለ እስራኤላውያን ይናገራል፤ አዲስ ኪዳን ግን ስለ አንድ ሰው - ስለኢየሱስ ክርስቶስ ይናገራል። ስለዚህ መላው አዲስ ኪዳን ከክርስቶስ ምጽአት እስከ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት ይናገራል ማለት ነው። አዲስ ኪዳን በሥነ ጽሑፋዊና ትምህርታዊ ይዘቱ ወንጌል፣ ታሪክ፣ መልእክትና ትንቢት ተብሎ ከአራት ይከፈላል።
ወንጌል ማለት የምሥራች ቃል ነው። ይህም ወንጌል ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

«ይህም ወንጌል በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ በኃይል የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስለ ተገለጠ ስለ ልጁ ነው፤ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።» ሮሜ ፩፣፫-፬።

Friday, September 7, 2012

በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ


ይህን ቃል የምናገኘው በመዝሙረ ዳዊት መዝ ፷፭፣ ቁጥር ፲፩ ላይ ነው።  «በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።» በግዕዙ «ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ - የምሕረትህን ዓመት አክሊል ትባርካለህ» ይላል።
በቸርነትህ፡- እግዚአብሔር የዓለማት እና የዘመናት ፈጣሪ፡ ብቻ ሳይሆን አስተዳዳሪም ነው። ዓለማት የተፈጠሩት፣ ዘመናት የሚቆጠሩት በቸርነቱ ነው። ማንም ሰው በዚህ ሃገር፣ በዚህ ዘመን ልፈጠር ብሎ ሃሳብ አላቀረበም። የሕልውናችን ምንጩ ቸርነቱ ነው። የተፈጥሮ ዑደት፣ የዘመናት መፈራረቅ፡ የዕፅዋት ዕድገት፣ የእንስሳት ሕይወት… ሁሉ የቸርነቱ ውጤት ነው። አንድ መምህር «ክረምቱ የሚገባው በባለሥልጣኖች ፊርማ ቢሆን ኖሮ ዝናብ ሳይጥል ኅዳር ታኅሳስ ይሆን ነበር።» ብሏል፤ እግዚአብሔር ከመላው ፍጥረት እና ከሕይወት ጋር የተያያዙትን ነገሮች በራሱ ብቻ ቁጥጥር ሥር አድርጓቸዋል። ፀሐይ የምትወጣው፣ ክረምት የሚገባው፣ እህሉ የሚበቅለው…. በቸርነቱ ነው። እኛ ክፉ ብንሆንም፣ በኃጢአት ብንጸናም፡ የእርሱ ቸርነት አልተቋረጠችም። የእግዚአብሔርን መጋቢነት ከኛ ደግነት/ክፋት ጋር የሚያገናኘው ነገር ስለሌለ እርሱ ሁልጊዜም ፍጥረቱን መመገቡን አያቋርጥም። እግዚአብሔር ሰውን ፈጥሮ ሰውም እየበዛ ሲሄድ በዚያው ልክ ክፋቱ በመብዛቱ በኖኅ ዘመን አንድ ጊዜ ምድርን ካጠበ በኋላ የተናገረው ቃል እንዲህ ይላል፡-
«በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፥ ብርድና ሙቀት፥ በጋና ክረምት፥ ቀንና ሌሊት አያቋርጡም።» ዘፍ ፰፣፳፪።
የሰው ልጅ ክፋት ቢበዛም ቸርነቱ እንዳልተቋረጠች ያሳያል፤ አሁንም እንደዚያው ነው። እርሱ እግዚአብሔር አይለወጥምና። ዛሬም ቸርነቱ ስላልተቋረጠ ሕልውናውን ለካዱት እንኳ ሳይቀር ፀሐይን ያወጣል፣ ዝናብን ያዘንባል።
«…እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና።» ማቴ ፭፣፵፭።
የቸርነቱን ነገሮች ዘርዝረን አንጨርሰውም።

Thursday, August 30, 2012

መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢትና የዓለም ፍጻሜ-ክፍል ፪


ባለፈው ክፍል የዓለምን ፍጻሜ አመላካች የሆኑ ከአሁን ቀደም እኔ ክርስቶስ ነኝ ብለው የተነሱ ሃሰተኞችን እንዲሁም በየቦታው እስከዛሬ የተካሄዱ ጦርነቶችን መረጃዎች ማየታችን ይታወሳል። ዛሬም ይህንኑ መረጃ ከመጽሐፍ ቅዱስ ምን ያህል እየተፈጸመ እንደሆነ እናያለን።
ማቴ ፳፬፣፯… ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤
ራብም፡
ከየትኛውም ዘመን ይልቅ በያዝነው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች በተለይ በታዳጊ ሃገሮች የሚገኙ ወገኖች በከፍተኛ ደረጃ በረሃብ እየተጠቁ መሆኑ ከማንም የተሰወረ አይደለም። የዓለማችን የሃብት ክፍፍል እና የሕዝቦች ስብጥር ሲነጻጸር ምን ያህል ፍትሐዊ እንዳልሆንን ያሳያል። መረጃዎች እንደሚያሳዩት 80%  የሚሆነው የምድራችን ሃብት 20% በሆነው የዓለም ሕዝብ እጅ ይገኛል። የሚከተሉት እውነታዎች የዓለም የምግብ ፕሮግራም /World Food Program/  በተለያዩ ጊዜያት ካወጣቸው መረጃዎች የተወሰዱ ናቸው።
-      እ.ኤ.አ በ2009 ዓ/ም ከአንድ ቢሊየን በላይ የሚሆን ሕዝብ በቂ ምግብ ማግኘት አልቻለም። ይህም ማለት የአሜሪካ፡ የአውሮፓ እና የካናዳ ሕዝብ ቢደመር እንኳ ይህን ያህል አይሆንም። በወቅቱ ከዓለማችን ከ6 ሰው አንዱ ለረሃብ የተጋለጠ ነበር ማለት ነው፡፡ ከእነዚህም 90 በመቶ በላይ የሚገኘው በታዳጊ ሃገራት ውስጥ ነው።
-      ከምግብ እጥረት ጋር በተያያዘ ምክንያት በየቀኑ 25 ሺ ሕጻናት እና ወጣቶች ለህልፈት ይዳረጋሉ።
-      ከግማሽ በላይ የሚሆነው የዓለም ሕዝብ የሚኖርባቸው እስያ እና የፓሲፊክ አካባቢዎች በዓለም ከሚገኙት በረሃብ ከተጠቁት 2/3 ኛው ይገኝባቸዋል።
-      በአሁኑ ሰዓት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት /malnutrition/ ከኤች አይ ቪ/ኤድስ፡ ከቲቢ እና ከወባ ከሶስቱም ድምር በላይ ሕጻናትን እየቀጠፈ ያለ የዓለማችን ችግር ነው። ከአራት ሕጻናት አንዱ የተመጣጠነ ምግብ አያገኝም። በታዳጊ ሃገራት ከ10 ሚሊየን በላይ ለሚሆነው የሕጻናት ሞት 60 በመቶ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ከ9 ሚሊየን በላይ ለሆነው ከአምስት ዓመት በታች ባሉ ሕጻናት ለደረሰው የሞት አደጋ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ይህ ማለት በየ6 ሴኮንድ አንድ ሕጻን ይሞታል ማለት ነው።
-      ከዓለማችን ሕዝብ ከ7 ሰው አንዱ ራቱን ሳይበላ ይተኛል።…….

Sunday, August 26, 2012

የጥያቄ፩- መልስ


 1.  እግዚአብሔር  አዳምን  ከመፍጠሩ  በፊት  አዳም  እንደሚሳሳት ያውቃል/አያውቅም?  እንደሚሳሳት  ካወቀ ለምን  ፈጠረው?  
  ወደጥያቄው መልስ ከመግባታችን በፊት ስለእግዚአብሔር ና ስለ ሰው ባሕርያት በጥቂቱ ማወቅ  ያለብን ጉዳይ አለ። እግዚአብሔር የማይመረመር፡ ልዑልና ኃያል አምላክ ስለሆነ ስለራሱ የገለጠልንን ያህል ብቻ እናውቃለን እንጂ ሙሉ በሙሉ ልንደርስበት አንችልም። የሰው ልጅ በሁለንተናው ውሱን ነው። ዓይናችን የሚያይበት፡ ጆሮአችን የሚያደምጥበት፡ እጃችን የሚዘረጋበት…. ሁለንተናችን ገደብ አለው።   ስለፈጣሪ ማወቅ አይደለም ስለፍጥረታት እንኳን ገና ያልደረስንባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ስለሆነም በአስተሳሰባችን ተነስተን የእግዚአብሔርን ሃሳብና አሠራር እንዲህ ቢሆን እንዲህ ይሆናል ብለን የራሳችን ግምት ልንወስድ አንችልም። ከውስንነታችን የተነሳ።

Friday, August 17, 2012

ጥያቄ-፩


    /ሜ የቀበ/
ይህ ክፍል መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆኑ ጥያቄዎችን የምንወያይበት ነው። 
    
      ፩. እግዚአብሔር  አዳምን  ከመፍጠሩ  በፊት  አዳም  እንደሚሳሳት ያውቃል/  አያውቅም? እንደሚሳሳት  ካወቀ ለምን  ፈጠረው?  
    
     ለዚህ ጥያቄ ተሳታፊዎች ከዚህ ጽሑፍ ሥር comments የሚለውን በመጫን post comment በሚለው  መላክ ትችላላችሁ። 

Thursday, August 9, 2012

ሚዛናዊነት

Mizanawinet, sebket, READ IN PDF


የሕይወታችን መመሪያ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን ስናጠና ከምንረዳቸው ታላላቅ ቁምነገሮች አንዱ ሚዛናዊነት ነው።በውስጡ ታሪካቸው ስለሰፈረላቸው ሰዎች መልካም ተግባር ሲነግረን ደካማ የሕይወት ክፍላቸውንም ያስነብበናል።
ለምሳሌ፡-
o   የአብርሃም የእምነት አባትነትና  ------በእግዚአብሔር ፊት የነበረበትን መንፈሳዊ ድክመት
o   የዳዊትን እንደልቤነትና ----- የዝሙት ውድቀት
o   የሙሴን ጠንካራ መሪነትና---- የእምነቱን መዛል  እናነባለን።
ከውድቀታቸው እንድንማር ብርታታቸውን አርአያ እንድናደርግ መንፈስ ቅዱስ ይህን አድርጓል።
በእኛ ዘንድ ግን እንዲህ አይደለም። ብናወራና ቢወራልን የምንወደው የበረታንበትን ነገር ብቻ ነው። ለዚህም ይመስላል ቆመው አይደለም ሞተው እንኳ ስለድክመታቸው እንዲወራ በማይፈልጉ ሰዎች ምክንያት በየቀብር ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የሚነበበው የሕይወት ታሪክ የጥቂት እውነትና የብዙ ውሸት ድምር ውጤት የሚሆነው።

ክርስቲያን ግን የእውነትና የማመዛዘንን በረከት የተረዳ ነው።
በአዲስ ኪዳንም ከኃጢአት በቀር በክርስቶስ ሕይወት የምንመለከተው ይህንኑ ነው።
o   የብዙዎችን የልብ ስብራት ከአፉ በሚወጣው የሕይወት ቃል ጠግኗል።  ----- ባልተቀበሉትና ባላወቁት አፍም ተሰድቧል።
o   በምራቁ  አፈር ለውሶ በደረቅ ግንባር ላይ ዓይን ፈጥሯል። ----- ርኅራሄ በሚነበብበት ፊቱ ላይም ምራቅ ተተፍቶበታል።
o   ጎባጣ አቅንቷል። ----- ጀርባው እስኪላጥ ተገርፎአል
o   የሞቱትን ከመግነዝ ፈትቶ ከመቃብር አስነስቷል። ------ በአደባባይ ተሰቅሎ ስለሁላችንም ሞቷል።
ይህም (ሚዛናዊነት) በቃሉ ውስጥ ያለማዳለል ሰፍሮልናል።
   ብዙ ሕመምን ያስከተሉ ነገሮች ያላቸው መልካም ጎን ቢታወቅ ኖሮ ሀሴትን ይፈጥሩ ነበር። ሁሉም ነገር መልካምና መጥፎ ጎን ሲኖረው ቁም ነገሩ ያለው ግን ነገሮችን በመልካም ጎናቸው መጠቀሙ ላይ ነው። የአንድ ነገር ገጽታ እንደ ተመለከትንበት አቅጣጫ ይወሰናል። ስለዚህ ነገሮችን በሚዛናዊነት እንመልከታቸው።
                               « በሚጠሉኝ መሀል የሚወደኝን አገኘሁት» ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ- ገጽ
                                                                                           በዲ/ ኢዮብ ይመር
የአንድን ነገር ሙሉ ገጽታ የምናገኘው ከሁሉም አቅጣጫ (በሚዛናዊነት) ስንመለከተው ነው።
በሥነ-ሕንጻ ትምህርት አራት መሠረታዊ እይታዎች አሉ፡ - የፊትለፊት፡ የጎን፡ የላይና የውስጥ (Front, side, top and section views) ስለዚያ ሕንጻ የተሟላ ስእል (ምስል) ለማግኘት እነዚህን አራቱንም አቅጣጫዎች  በሙሉ ማየትና መረዳት ያስፈልጋል።
ተፈጥሮአችን ራሱ ሚዛናዊ እንድንሆን ያስተምረናል። ሁላችንም በተቃራኒ  አቅጣጫ የተቀመጡ ሁለት ጆሮዎች አሉን። አእምሮአችን (ሕሊና) እና አንደበታችን (አፍ) ግን አንድ ነው። ስለአንድ ጉዳይ ተቃራኒ የሆኑ ብዙ ነገሮችን ልንሰማ እንችላለን።
 ስለአንድ ነገር በአንደበታችን ከመናገራችን በፊት ነገሮችን በማስተዋል አመዛዝነን ከግራ ከቀኝ መርምረን ቢሆን አድማጭን ከሚያቆስል ንግግር እንጠበቃለን፡ ራሳችንንም ከፍርድ እንጠብቃለን።
በስፍራም፡ በአቅጣጫም  የማይወሰነው እግዚአብሔር  ከላይ ሆኖ ሁሉን ፍጹም በሆነ ሚዛናዊነት ይመለከታል። እኛ በየተመለከትንበት አቅጣጫ ፍርድን ብናዛባ፡ ሁሉም በእርሱ ፊት ግልጽ ነውና በፍትሐዊነቱ ፍርድን ያደላድላል።
ስለዚህ በምንሰማቸው ብዙ ነገሮች ሚዛናዊነት ይኑረን።  ሳናመዛዝን ለመናገርም አንቸኩል። ሁላችንም ሁሉም በእግዚአብሔር ፊት በግልጽ የሚታይ ነውና።
« እግዚአብሔር በሰማይ አንተም በምድር ነህና በአፍህ አትፍጠን። በእግዚአብሔርም ፊት ቃልን ይናገር ዘንድ ልብህ አይቸኩል፡ ስለዚህም ቃልህ ጥቂት ትሁን።» ምሳ ፭፡፪።