Friday, October 19, 2012

ብሉይ ኪዳን - የኦሪት ክፍል


በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ተከታታይ ትምህርታችን ባለፉት ጊዜያት ለጥናታችን የሚያስፈልጉንን ነጥቦች ካየን በኋላ ለአጠቃላይ ግንዛቤ የብሉይ ኪዳንን እና የአዲስ ኪዳንን ጠቅለል ያለ ታሪካዊ ዳሰሳ ተመልከተናል። በቀጣይ የመጽሐፍ ቅዱስ ሁለቱ ኪዳናት በተከፋፈሉባቸው ሥነ-ጽሑፋዊ ይዘት ቅደም ተከተል መሠረት እያንዳንዳቸውን በየተራ እንመለከታለን።
ብሉይ ኪዳን በሥነ-ጽሑፋዊ ይዘቱ በአራት እንደሚከፈል ቀደም ብለን ተመልክተናል። እነዚህም፡
፩. ሕግ፡ - ከኦሪት ዘፍጥረት - ኦሪት ዘዳግም --- ፭ መጻሕፍት
፪. ታሪክ ፡- ከመጽሐፈ ኢያሱ ወልደ ነዌ- መጽሐፈ አስቴር-- ፲፪ መጻሕፍት
፫. ጥበብ፡-  ከመጽሐፈ ኢዮብ- መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን-- ፭ መጻሕፍት
፬. ትንቢት፡- ከትንቢተ ኢሳይያስ - ትንቢተ ሚልክያስ---፲፯ መጻሕፍት ናቸው።
ለዛሬ የሕግ ክፍል የሆነውን አምስቱን የኦሪት መጻሕፍት ጠቅለል አድርገን እናያለን።
ኦሪት የሚለው ቃል አራይታ ከሚለው የጥንት የሶርያ ቋንቋ እንደተገኘ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ይናገራል። ትርጉሙም ሕግ፣ ትምህርት ማለት ነው። ይህም ሕግ ወይም ትእዛዝ ከእብራይስጡ ቶራህ ከሚለው ቃል እንደተገኘም ምሁራን ይናገራሉ። የሕግ ክፍል የተባለው የኦሪት መጻሕፍት ኦሪት ዘፍጥረት፣ ኦሪት ዘጸአት፣ ኦሪት ዘሌዋውያን፣ ኦሪት ዘኊልቁ እና ኦሪት ዘዳግም የተባሉትን የመጀመሪያ አምስት መጻሕፍት ያጠቃልላል። አምስቱ የኦሪት መጻሕፍት ፔንታቱክ በመባልም ይታወቃሉ። አሁን ድረስ የአይሁድ እምነት ተከታዮች ዋና መጻሕፍቶቻቸው እንደሆኑ ይነገራል።
አምስቱ የኦሪት መጻሕፍት በአብዛኛው የተለያዩ ነገሮችን አጀማመር ይገልጹልናል። ከእነዚህም፡-
የፍጥረትን አጀማመር -የሰማይን የምድርን እና በውስጡ የሚገኙ ሕይወት ያላቸው ፍጥረታት ጅማሬ፣
በአዳምና በሔዋን መፈጠር መላው የሰው ዘር እንዴት እንደተባዛ እና ምድርን እየሞላ እንደሄደ፣
ኃጢአት እንዴት ወደዓለም እንደገባ እና ሰው እግዚአብሔርን ማምለክ እንዴት እንደተወ፣
እግዚአብሔር ከሰው ጋር ያለውን ግንኙነት ለማደስ ከኖኅ፣ ከአብርሃም ጋር ቃል ኪዳን እንደጀመረ፣
በብሉይ ኪዳን ዋና የታሪክ ባለቤት የሆኑት የእስራኤል ሕዝብ አመጣጥ እንዴት እንደተጀመረ፣
የተጻፈ ሕግ፣ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ጋር ባለው ግንኙነት ሊጠብቃቸው የሚገቡ በርካታ ሥርዓቶች…. ወዘተ አጀማመር ይገልጻል።
በኦሪት መጻሕፍት ውስጥ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያደረገለትን እንክብካቤ እና ትድግና፡ ሕዝቡም ለእግዚአብሔር ሊፈጽሙ የሚገባቸውን ሥርዓትና ቅድስና ይዘረዝራል። የተሰጡት ሕግና ሥርዓቶች በጣም በርካታ፡ በዝርዝር እና ሁለመናቸውን የሚመለከት ነበረ። በሁለንተናቸው አምላካቸውን በቅድስና እንዲመስሉ ለእርሱ የተለየ ሕዝብ እንዲሆኑ ስለእያንዳንዱ የሕይወት ክፍላቸው በዝርዝር እና በጥልቅ ተነግሯቸዋል። አብዛኛው የኦሪት ክፍል ለጊዜው አሰልቺ የሚመስል በኋላ ግን ጠቃሚነቱ የሚጎላ በበርካታ ዝርዝር ሕግጋትና ሥርዓት የተሞላ ታሪካዊ ፍሰት ያለው ክፍል ነው።

Tuesday, October 16, 2012

Quotes vs Bible Quotes-1

Write your plans in pencil but give God the eraser. 
                                                                                            --Unknown
-      በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፥ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ :: ምሳ ፫: ፭
  
   Learn as if you were going to live forever.
   Live as if you were going to die tomorrow.
                                                                           
--Mahatma Gandhi
         ንደሚኖር የሰራን; ንደሚሞት ንዘጋጅ:: 
      
-      አሁንም። ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን የምትሉ እናንተ፥ ተመልከቱ፥ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና። ያዕ ፬: ፲፫
      


If you give 100%, God will make up the difference!
                                                               --  Anonymous
-      አሳቤ እንደ አሳባችሁ መንገዳችሁም እንደ መንገዴ አይደለምና ይላል እግዚአብሔር፦ ኢሳ ፶፭:፰
    
      "Seven days without work make one weak"  ......... somebod
                                                             … ሥራ ፈትታችሁ ቀኑን ሁሉ በዚህ ስለ ምን ትቆማላችሁ? አላቸው። ማቴ፳


….ደግሞ ከእናንተ ጋር ሳለን። ሊሠራ የማይወድ አይብላ ብለን አዘናችሁ ነበርና።
 ፪ተሰ፫፡፲

    The things I want to know are in books;
    My best friend is the man who'll get me a book I didn't read.
                                                                                                   --Abraham Lincoln (1809-1865)
-      ይህም ከጌታ ዘንድ ሆነ፥ ለዓይኖቻችንም ድንቅ ነው የሚለውን ከቶ በመጽሐፍ አላነበባችሁምን?  ማቴ፳፩፡፵፪
    


                                         


Thursday, October 4, 2012

ፍልስጥኤምና ዙርያዋ

Plestine map, read in pdf
ባለፈው ካርታ ከተመለከትነው ከኖኅ ልጆች ምድርን መከፋፈል በኋላ ብዙ ተባዙ ምድርም ሞሉአት ተብሎ በተነገረው አምላካዊ ቃል መሠረት የሰው ዘር እየበዛ እየተባዛ ሄደ። ይሁን እንጂ የመጽሐፍ ቅዱስ ትኩረትና ዋና መልእክት ስለመላው ዓለም ሕዝቦች ታሪክ መዘገብ ሳይሆን ስለአንድ ሕዝብ ስለእስራኤላውያን በኋላም ከእነርሱ ስለሚገኘው ስለአንድ ሰው ስለኢየሱስ ክርስቶስ በመሆኑ የታሪክ ፍሰቱ ከመካከለኛው ምሥራቅ አልወጣም። በዚህም ምክንያት መካከለኛውን ምሥራቅ በጥልቀት ማየት ያስፈልጋል። ከዚህ በታች የምንመለከተው ፫ኛ ካርታ ይህንን የመካከለኛውን ምሥራቅ የቀድሞ ዘመን አገሮች ያሳየናል።

ከካርታው እንደምንመለከተው ይህ የቀድሞው ዘመን የእስራኤል እና የዙርያዋ አገር በተራሮች፣ በወንዞች፣ በበረሃ፣ በባሕር፣ በሜዳም… የተሞላ ሁሉም የመልክአ ምድር ገጽታዎች የሚገኝበት ነው።
ፍልስጥኤም፣ ፍልስጥኤማውያን በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት መግለጫ መሠረት ከካም ነገድ የመጡ በደቡብ ከነዓን በባሕር (በታላቁ ባሕር) ዳር ባለው ሜዳ የነበሩ ሕዝቦች ናቸው። 
ፍልስጥኤማውያን እየበዙና እየበረቱ ሲሄዱ አካባቢያቸውን ሁሉ በመቆጣጠራቸው መላው ከነዓን ፍልስጥኤም እየተባለ ይጠራ ነበር። እስራኤላውያን ከግብጽ ምድር በሙሴ መሪነት መጥተው ይህችን ምድር ሊወርሱ ሲሉ ፍልስጥኤማውያንን ፈርተው በዙርያ መንገድ ወደ አገራቸው ገብተዋል። /የእስራኤላውያንን ጉዞ በቀጣዩ ክፍል ፬ ካርታ እንመለከታለን።/
በዚህ ካርታ ወደፊት በተያያዥነት ከምናያቸው ታሪኮች ውስጥ የሚከተሉት ጥቂቶቹ ናቸው።
፩. በዘመነ ቀደምት አበው አብርሃም በፍልስጥኤም ምድር በእንግድነት መኖሩ፡ ዘፍ ፳፩፣ ፳፪-፴፬።
፪. በዘመነ መሳፍንት መጨረሻ ፍልስጥኤማውያን እስራኤላውያንን መዋጋታቸው፣ ታቦቱን መማረካቸው ፩ሳሙ ፬-፭።
፫. በዘመነ ነገሥት ዳዊት ፍልስጥኤማዊ የነበረውን ጎልያድን ድል ማድረጉ ፩ሳሙ ፲፯. ወዘተ….  
ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ሁሉንም በየቦታቸው ስንደርስ እናያቸዋለን።
ይቆየን።



Wednesday, September 26, 2012

ብርሃን ይሁን፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር የመጀመሪያው ቃል (ንግግር)
Birhan Yihun, sebket, READ IN PDF
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ ብርሃንም ሆነ። ዘፍ ፩፡፫
በመጽሐፍ ቅዱሳችን በመጀመሪያው መጽሐፍ በመጀመሪያው ምዕራፍ እግዚአብሔር በመጀመሪያ የተናገረው ቃል ብርሃን ይሁን የሚል ነው። ከዚያ በፊት ባሉት ቁጥሮች በዝምታ (በአርምሞ) ሲሠራ ቆይቷል። ሰማይ፡ ምድር፡ ጨለማ፡ መላእክት…. የተፈጠሩት በዝምታው ነው። እግዚአብሔር በዝምታውም ይሠራል። በኀልዮ ይላሉ፡፡ ሲያስብ ይፈጸማል፡ ይከናወናል። የሰው ሃሳብ ምናባዊ የሆኑ ብዙ ነገሮችን ሊያወጣ ሊያወርድ ይችላል። እግዚአብሔር ግን በሃሳቡ ብቻ ተጨባጭ ነገሮችን ያስገኛል።  ታላላቆቹና የፍጥረታት መሠረታውያን የተባሉት ፬ቱ ባሕርያት እሳት፡ ነፋስ፡ ውኃ፡መሬት የተፈጠሩት በኀልዮ፡ (በዝምታ) ነው።
እግዚአብሔር በምን ተናገረ?
እግዚአብሔርም፦ ብርሃን ይሁን አለ። እግዚአብሔርም… አለ። ይህ የተናገረበት ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነው አካላዊ ቃል ወልድ በኋላም ሰው የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። እግዚአብሔር በሦስትነቱ ሥላሴ ሲባል አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው። ሥላሴ በአብ ልብነት ያስባሉ፡ በወልድ ቃልነት ይናገራሉ፡ በመንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሕያው ሆነው ይኖራሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር ዓለምን ሲፈጥር የተናገረበት ቃል ወልድ ነበረ።
በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ዮሐ ፩፡ ፩።
ያ ቃል ወልድ በሐዲስ ኪዳን ሥጋን ለብሶ ሰው የሆነው፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው፡ ዓለምን ሁሉ ያዳነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።  ….. ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ዮሐ ፩፡ ፲፬።

ዛሬ እግዚአብሔር በምን ይናገራል?  
- በብሉይ ኪዳን በዝምታ፡ በሕልም፡ በራእይ፡ በነቢያት፡…. በወልድ ቃልነት ይናገር ነበር።
ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ዕብ ፩፡፩
-በሐዲስ ኪዳን የሚያናግርበት መንገድ አንድ ብቻ ነው።
ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን።  ዕብ ፩፡፪
እንግዲህ እግዚአብሔር ዛሬ እኛን የሚያናግረን በዚያው ቃል - በወልድ - በኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህንም የምናውቀው በተጻፈው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ እና በመምህራን አማካይነት ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር የሚያናግረንን ለማወቅ፡ ብሎም ለመታዘዝ ቃሉን - ይሄውም ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን እና መጽሐፍ ቅዱስን - ማወቅ አለብን ማለት ነው። ይህ ቃሉ ዓለምን የፈጠረ - ፈጣሪ፡ ዓለምንም ያዳነ - አዳኝ ዛሬም የእኛን ሐይወት ያዳነ- የሚሠራ አካላዊ ቃል ነው። እግዚአብሔር ሲያናግረን ልናዳምጥና ልንጠቀምበት ይገባል።

Monday, September 17, 2012

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካዊ ዳሰሳ - አዲስ ኪዳን


ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናታችን አጠቃላይ ግንዛቤ ይረዳን ዘንድ በሁለቱ ኪዳናት ያሉትን ታሪኮች ጠቅለል አድርገን ለማየት የብሉይ ኪዳንን ታሪካዊ ፍሰት ባለፈው ትምህርታችን ማየታችን ይታወሳል። ለዛሬ የአዲስ ኪዳንን አጠቃላይ ይዘት እንዲሁ እንመለከታለን።
አዲስ ኪዳንን አዲስ ያሰኘው ብሉይ ኪዳን ያለፈ፣ ያረጀ ወይም የቆየ ስለሆነ ነው። ብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ጋር የገባው ቃል ኪዳን ሲሆን በእነርሱ አለመታዘዝ ምክንያት ኪዳኑ ሊጸኛ አልቻለም።
«ፊተኛው ኪዳን ነቀፋ ባይኖረው፥ ለሁለተኛው ስፍራ ባልተፈለገም ነበር።…. አዲስ በማለቱ ፊተኛውን አስረጅቶአል፤ »  ዕብ ፯፣ ፯ና ፲፫።
እስራኤላውያን እንታዘዛለን ብለው ቃል የገቡበትን ሕግ ሊያከብሩ ባለመቻላቸውና ሕጉን በመጣሳቸው እግዚአብሔር በዚያው በብሉይ ኪዳን ዘመን ሌላ አዲስ ኪዳን እንደሚመሠርት መናገሩን ካሁን ቀደም ጠቅሰን መማማራችን ይታወሳል። ዘጸ ፳፬፣፯።
« እነሆ፥ ከእስራኤል ቤትና ከይሁዳ ቤት ጋር አዲስ ቃል ኪዳን የምገባበት ወራት ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር
ከግብጽ አገር አወጣቸው ዘንድ እጃቸውን በያዝሁበት ቀን ከአባቶቻቸው ጋር እንደ ገባሁት ያለ ቃል ኪዳን አይደለም እነርሱ በኪዳኔ አልጸኑምና፥ እኔም ቸል አልኋቸው፥ ይላል እግዚአብሔር፦ ኤር ፴፩ ፣ ፴፩ - ፴፬
አዲስ ኪዳን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን መላውን ዓለም /የሰው ዘር የሚመለከት እግዚአብሔር በልጁ ሞት ለሰው ያደረገው የቸርነቱን ሥራ የሚያሳይ ኪዳን ነው።
እንዲሁም ከእራት በኋላ ጽዋውን አንሥቶ እንዲህ አለ፦ ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው። ሉቃ ፳፪፣፳።
ካሁን ቀደም እንዳየነው ብሉይ ኪዳን ስለአንድ ሕዝብ - ስለ እስራኤላውያን ይናገራል፤ አዲስ ኪዳን ግን ስለ አንድ ሰው - ስለኢየሱስ ክርስቶስ ይናገራል። ስለዚህ መላው አዲስ ኪዳን ከክርስቶስ ምጽአት እስከ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት ይናገራል ማለት ነው። አዲስ ኪዳን በሥነ ጽሑፋዊና ትምህርታዊ ይዘቱ ወንጌል፣ ታሪክ፣ መልእክትና ትንቢት ተብሎ ከአራት ይከፈላል።
ወንጌል ማለት የምሥራች ቃል ነው። ይህም ወንጌል ራሱ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

«ይህም ወንጌል በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ በኃይል የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስለ ተገለጠ ስለ ልጁ ነው፤ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።» ሮሜ ፩፣፫-፬።

Friday, September 7, 2012

በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ


ይህን ቃል የምናገኘው በመዝሙረ ዳዊት መዝ ፷፭፣ ቁጥር ፲፩ ላይ ነው።  «በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል።» በግዕዙ «ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ - የምሕረትህን ዓመት አክሊል ትባርካለህ» ይላል።
በቸርነትህ፡- እግዚአብሔር የዓለማት እና የዘመናት ፈጣሪ፡ ብቻ ሳይሆን አስተዳዳሪም ነው። ዓለማት የተፈጠሩት፣ ዘመናት የሚቆጠሩት በቸርነቱ ነው። ማንም ሰው በዚህ ሃገር፣ በዚህ ዘመን ልፈጠር ብሎ ሃሳብ አላቀረበም። የሕልውናችን ምንጩ ቸርነቱ ነው። የተፈጥሮ ዑደት፣ የዘመናት መፈራረቅ፡ የዕፅዋት ዕድገት፣ የእንስሳት ሕይወት… ሁሉ የቸርነቱ ውጤት ነው። አንድ መምህር «ክረምቱ የሚገባው በባለሥልጣኖች ፊርማ ቢሆን ኖሮ ዝናብ ሳይጥል ኅዳር ታኅሳስ ይሆን ነበር።» ብሏል፤ እግዚአብሔር ከመላው ፍጥረት እና ከሕይወት ጋር የተያያዙትን ነገሮች በራሱ ብቻ ቁጥጥር ሥር አድርጓቸዋል። ፀሐይ የምትወጣው፣ ክረምት የሚገባው፣ እህሉ የሚበቅለው…. በቸርነቱ ነው። እኛ ክፉ ብንሆንም፣ በኃጢአት ብንጸናም፡ የእርሱ ቸርነት አልተቋረጠችም። የእግዚአብሔርን መጋቢነት ከኛ ደግነት/ክፋት ጋር የሚያገናኘው ነገር ስለሌለ እርሱ ሁልጊዜም ፍጥረቱን መመገቡን አያቋርጥም። እግዚአብሔር ሰውን ፈጥሮ ሰውም እየበዛ ሲሄድ በዚያው ልክ ክፋቱ በመብዛቱ በኖኅ ዘመን አንድ ጊዜ ምድርን ካጠበ በኋላ የተናገረው ቃል እንዲህ ይላል፡-
«በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፥ ብርድና ሙቀት፥ በጋና ክረምት፥ ቀንና ሌሊት አያቋርጡም።» ዘፍ ፰፣፳፪።
የሰው ልጅ ክፋት ቢበዛም ቸርነቱ እንዳልተቋረጠች ያሳያል፤ አሁንም እንደዚያው ነው። እርሱ እግዚአብሔር አይለወጥምና። ዛሬም ቸርነቱ ስላልተቋረጠ ሕልውናውን ለካዱት እንኳ ሳይቀር ፀሐይን ያወጣል፣ ዝናብን ያዘንባል።
«…እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና።» ማቴ ፭፣፵፭።
የቸርነቱን ነገሮች ዘርዝረን አንጨርሰውም።

Thursday, August 30, 2012

መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢትና የዓለም ፍጻሜ-ክፍል ፪


ባለፈው ክፍል የዓለምን ፍጻሜ አመላካች የሆኑ ከአሁን ቀደም እኔ ክርስቶስ ነኝ ብለው የተነሱ ሃሰተኞችን እንዲሁም በየቦታው እስከዛሬ የተካሄዱ ጦርነቶችን መረጃዎች ማየታችን ይታወሳል። ዛሬም ይህንኑ መረጃ ከመጽሐፍ ቅዱስ ምን ያህል እየተፈጸመ እንደሆነ እናያለን።
ማቴ ፳፬፣፯… ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤
ራብም፡
ከየትኛውም ዘመን ይልቅ በያዝነው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች በተለይ በታዳጊ ሃገሮች የሚገኙ ወገኖች በከፍተኛ ደረጃ በረሃብ እየተጠቁ መሆኑ ከማንም የተሰወረ አይደለም። የዓለማችን የሃብት ክፍፍል እና የሕዝቦች ስብጥር ሲነጻጸር ምን ያህል ፍትሐዊ እንዳልሆንን ያሳያል። መረጃዎች እንደሚያሳዩት 80%  የሚሆነው የምድራችን ሃብት 20% በሆነው የዓለም ሕዝብ እጅ ይገኛል። የሚከተሉት እውነታዎች የዓለም የምግብ ፕሮግራም /World Food Program/  በተለያዩ ጊዜያት ካወጣቸው መረጃዎች የተወሰዱ ናቸው።
-      እ.ኤ.አ በ2009 ዓ/ም ከአንድ ቢሊየን በላይ የሚሆን ሕዝብ በቂ ምግብ ማግኘት አልቻለም። ይህም ማለት የአሜሪካ፡ የአውሮፓ እና የካናዳ ሕዝብ ቢደመር እንኳ ይህን ያህል አይሆንም። በወቅቱ ከዓለማችን ከ6 ሰው አንዱ ለረሃብ የተጋለጠ ነበር ማለት ነው፡፡ ከእነዚህም 90 በመቶ በላይ የሚገኘው በታዳጊ ሃገራት ውስጥ ነው።
-      ከምግብ እጥረት ጋር በተያያዘ ምክንያት በየቀኑ 25 ሺ ሕጻናት እና ወጣቶች ለህልፈት ይዳረጋሉ።
-      ከግማሽ በላይ የሚሆነው የዓለም ሕዝብ የሚኖርባቸው እስያ እና የፓሲፊክ አካባቢዎች በዓለም ከሚገኙት በረሃብ ከተጠቁት 2/3 ኛው ይገኝባቸዋል።
-      በአሁኑ ሰዓት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት /malnutrition/ ከኤች አይ ቪ/ኤድስ፡ ከቲቢ እና ከወባ ከሶስቱም ድምር በላይ ሕጻናትን እየቀጠፈ ያለ የዓለማችን ችግር ነው። ከአራት ሕጻናት አንዱ የተመጣጠነ ምግብ አያገኝም። በታዳጊ ሃገራት ከ10 ሚሊየን በላይ ለሚሆነው የሕጻናት ሞት 60 በመቶ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ከ9 ሚሊየን በላይ ለሆነው ከአምስት ዓመት በታች ባሉ ሕጻናት ለደረሰው የሞት አደጋ ምክንያቱ ይሄው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ነው። ይህ ማለት በየ6 ሴኮንድ አንድ ሕጻን ይሞታል ማለት ነው።
-      ከዓለማችን ሕዝብ ከ7 ሰው አንዱ ራቱን ሳይበላ ይተኛል።…….